በአፍሪካ የምጣኔ ሀብት እንቅስቃሴ ካልተስፋፋና፤ በተለይ ጎረቤት ሀገሮች ድንበሮቻቸውን ለስራና ለንግድ ክፍት ካላደረጉ፤ እድገታቸው ፈተና እንደሚገጥመውና፤ ወደ አውሮፓ የሚፈልሱ ሰዎች ቁጥርም እንደሚጨምር የዓለም ባንክ ፕሬዝደንት በዛሬውለት ገልጸዋል።
የሀገሮች ምጣኔ ሃብት ቅንጅትና ንግድን የሚያስፋፉ ፖሊሲዎች በአፍሪካ ሀገሮች በአሁኑ ወቅት አነስተኛ መሆናቸው አሳሳቢ እንደሆነ ጂም ዮንግ ኪም በዛሬውለት ለጋዜጠኞች አስታውቀዋል።
በትናንትናው ዝግጅታችን እንደዘገብንው የዓለም የገንዘብ ድርጅት አይ ኤም ኤፍ (IMF )የኢትዮጵያ ምጣኔ ሀብት በያዝነው የአውሮፓዊያን ዓመት ተቀዛቅዞ እንደሚቀጥል አስታውቋል። ባለፈው ዓመት 10.2 ከመቶ ያደገው ሀገራዊ ምርት ምጣኔ ወደ 4.5 ከመቶ ዝቅ ሲል፤ የዜጎችን የናንተን ኑሮና ኪስ እንዴት ይመለከታል? ዘጋቢያችን ሔኖክ ሰማእግዜር በዓለም ባንክና ሌሎች የልማት ተቋማት ከ30 ዓመታት በላይ የሰሩትን ዶር አክሎግ ቢራራ ለውይይት ጋብዟል።
በተጨማሪም ሔኖክ አመታዊውን የዓለም ባንክና የዓለም የገንዘብ ድርጅት ጉባዔ እየተከታተለ ነው። ከባልደረባችን ሰሎሞን አባተ ጋር በስልክ ተነጋግረዋል። ሙሉ ዝርዝሩን ለማዳመጥ የድምጽ ፋይሉን ይጫኑ።