በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ለዳግም እስር የተዳረጉት ጋዜጠኞች፣ጦማሪያኑና፣ፖለቲከኞቹ እንዲፈቱ የሰብዓዊ መብት ድርጅቶቹ እየወተወቱ ነው


የምሥጋና ቀን በተመስገን ደሣለኝ ቤተሰቦች ቤት - መጋቢት 16/2010 ዓ.ም፤ ጃሞ-አዲስ አበባ
የምሥጋና ቀን በተመስገን ደሣለኝ ቤተሰቦች ቤት - መጋቢት 16/2010 ዓ.ም፤ ጃሞ-አዲስ አበባ

ከዕሁድ መጋቢት 16/ 2018 ዓ.ም ጀምሮ በንፋስ ስልክ ፖሊስ መምሪያ በቁጥጥር ሥር በእስር የሚገኙት ዐሥራ አንድ ጋዜጠኞች፣ የኢንተርኔት አምደኞችና የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች በአስቸኳይ እንዲፈቱ ዐርባ አንድ ዓለም አቀፍና አሕጉር አቀፍ የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች ጠየቁ። ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ዛሬ ሆስፒታል ገብቶ እንደነበረም ቤተሰቦቹ ገልፀዋል።

የሰብዓዊ መብት ድርጅቶቹ እስረኞቹ እንዲፈቱ እየወተወቱ ነው
please wait

No media source currently available

0:00 0:09:24 0:00

መቀመጫውን ጄኔቫ፣ ስዊዘርላንድ ያደረገው 'ስብስብ ለሰብኣዊ መብቶች በኢትዮጵያ' ተብሎ የሚጠራ የሰብዓዊ መብት ድርጅትና ዋና ዳይሬክተር አቶ ያሬድ ኃይለማርያምና የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ፕሮጀክት አስተባባሪ ወ/ት ሶሊያና ሽመልስ ለአሜሪካ ድምፅ ስለ ድርጅቶቹ መግለጫ ሲናገሩ ፤መንግሥት የፖለቲካ ምሕዳሩን ለማስፋትና በሀገሪቱ የተከሰተውን ቀውስ ለማርገብ በሚል የፈታቸውን እስረኞች መልሶ ማሰሩን ለፖለቲካ ምሕዳሩም ኾነ ለሰብዓዊ መብት እንቅስቃሴው አስፈሪ መሆኑ ያሳሰባቸው ድርጅቶች እንደሆኑ ተናግረዋል።

እሁድ መጋቢት 16/2010 ዓ.ም በአዲስ አበባ በተመስገን ደሣለኝ ቤተሰቦች የጀሞ ኮንደሚኒየም መኖሪያ ቤት በተዘጋጀው የምስጋና ዝግጅት ላይ ተይዘው የታሰሩት ዐሥራ አንድ ሰዎች መካከል እስክንደር ነጋ፣ ተመስገን ደሳለኝ፣ ዘላላም ወርቃገኘሁ፣ በፍቃዱ ሀይሉ፣ማህሌት ፋንታሁና ይድነቃቸው አዲስ ጋዜጠኞችና የኢንተርኔት ላይ አምደኖች መሆናቸውን አስታውቋል።

ከእነዚህ ውስጥም በጣም በቅርቡ ከእስር የተፈታውን ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋን ጨምሮ ሁሉም ከዚህ ቀደም በተለያየ ጊዜ ታስረው የተፈቱ ናቸው።

በተጨማሪም እንዲሁ በቅርቡ የተፈታው የቀድሞ የአንድነት ፓርቲ አመራር የነበረው አቶ አንዷለም አራጌን ጨምሮ ወይንሸት ሞላ፣አዲሱ ጌትነት፣ስንታየሁ ቸኮልና ተፈራ ተስፋዬም አበረው ሲሆኑ ይህ የምስጋና ዝግጅት ቀደም ሲል በእነ እስክንድር መኖሪያ ቤት የተዘጋጀ ቀጣይ ክፍል እንደሆነ ከአስተባብስሪ ኮሚቴዎች አንዷ ወ/ሮ መአዛ መሐመድ ይናገራሉ። እስረኞቹ በሀገሪቱ ውስጥ ዴሞክራሲና ፍትሕ እንዲሰፍን መስዋትነትን የከፈሉ በመሆናቸው ሊመሰገኑ ይገባል በሚል ዝግጅቱን እንዳዘጋጁ ወ/ሮ መአዛ ጨምረው ተናግርዋል።ይህ የምስጋና ዝግጅት በመደረጉ ምክኒያትም ለእስር ተዳርገው በአሁኑ ሰዓት ከሌሎች ከ80 በላይ በሆኑና

በአስቸኳይ ጊዜ ዐዋጁ ምክኒያት ከሰበታ አካባቢ ከታሰሩ ወርጣቶች ጋራ እጅግ በተፋፈገ ሁኔታ ታስረው እንደሚገኙ ቤተሰቦቻቸው ገልፀዋል። እስረኞቹን ሊጠይቋቸው ሲሄዱ ታስረውበት የሚገኙበት ሁኔታ ሰው ሊኖርበት የሚችል አይደለም እንዳሏቸው ገልፀውልናል።

የጋዜጠኛ ተምስገን ደሳለኝ ወንድም ታሪኩ ደሳለኝ በድጋሚ የታሰረው ወንድሙ ቀድሞ የነበረበት የወገብ ሕመም በመባባሱ ምክኒያት ዛሬ ከታሰረበት ጣቢያ ወጥቶ ሆስፒታል ገብቶ እንደነበር ያስረዳል።

እስረኞቹ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ሲውሉ በዕለቱ በነበረው ዝግጅት ላይ ተሰቅሎ የነበረው አረንጓዴ ቀይ ቢጫ ባንዲራ በማን እንደተሰቀለ እንዲናገሩ በምርመራ ወቅት መጠየቃቸውንና በጉዳዮቸው ላይ የሚወስነው የአስቸኳይ ጊዜ ዐዋጁ የዕዝ ማዕከል ወይንም ኮማንድ ፖስቱ ነው መባሉን መዘገባችን ይታወሳል።

በዛሬው ዕለትም ታስረውበታል ወደ ተባለው ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ የማኅበረሰብ ፖሊስ መምሪያ ድውዬ ስልኩን ያነሱት ሰው ወደ አዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ደውዬ እንድጠይቅ ነግረውናል። አዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ደግሞ ስልክ ደግሞ ደጋግመን ብንሞክርም ሊነሳልን አልቻለም። በተጨማሪም ከፌደራል መንግስትና ከኮማንድ ፖስቱ ባለሥልጣናት መረJኣን ለማግኘት የእጅ ስልኮቻቸው ስለማይነሱ ሊሳካልን አልቻለም። ምላሽ እንዲሰጡን ጥረታችንን እንቀጥላለን።

የጋዜጠኞች ደህንነት ተሟጋች ቡድን (ሲፒጄ)የኢትዮጵያ ባለሥልጣናት እስረኞቹን እንዲለቀቁ መጠየቁን እንዲሁም ዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት አምነስቲ ኢንተርናሽናል “ከእስር የተለቀቁ ሰዎች በአጭር ጊዜ ውስጥ ተመልሰው መታሰር በአጠቃላይ ኢትዮጵያ የሚያስፈልጋት የሥርዓት ለውጥ መሆኑን ማሳያ ነው” ማለቱን መዘገባችን ይታወሳል።

የፌስቡክ አስተያየት መስጫ

XS
SM
MD
LG