ከጎበዝ ጊታር ተጫዋቾች ጀርባ ሌላ ታላቅ አርቲስት አለ የሚለው አባባል ለአንቶኒዮ አኮስታ ሳይሆን አይቀርም።የሚሰራችው የጊታር ክሮች በአለም አቀፍ ደረጃ ባሉ ሙዚቀኞች ምቹና ተወዳጅነትን ያተረፉ ናቸው።
የረቂቅ ሙዚቃ (classical music) ጊታር ተጫዋቾች ብዙውን ጊዜ የሚጠቀሙት የናይሎን (nylon) ክሮችን ነው። ምክንያቱም ለድምፅ ህብር፣ ለጣቶች ፍጥነት እንዲሁም ለድምፅ መጨመርና መቀነስ ምቹ ስለሆኑ።
መሰረቱ ደቡብ ስፔን የሆነው የፍላሜንኮ (flamenco) ሙዚቃ የራሱ የሆነ የዳንስና የአዘፋፈን ስልት አለው። ዋናው የፍላሜንኮ መለያው ደግሞ በጊታር የሙዚቃ መሳሪያ ላይ የተመሰረተ መሆኑ ነው። ብብዛት በጊታር አጨዋወት ላይ እንተለመደው የግራ እጅ ጣቶች ፍጥነትን ብቻ ሳይሆን የቀኝ እጅን ልዩ እንቅስቃሴና ፍጥነት የፍላሜንኮ ሙዚቃ ጨዋታውን የተለየ ያደርገዋል።
የቶኒ አኮስታ የጊታር ክሮች በነዚህ ሁለት የሙዚቃ ስልቶች ሙዚቃ ተጫዋቾቹ ዘንድ ተመራጭ ነው።
ቶኒ አኮስታ የክላሲካል ሙዚቀኛ፣ የንግድ ሰው፣ እንዲሁም የክላሲካልና የፍላሜንኮ የጊታር ክር አምራች ነው።
ያመረታቸው ክሮች በጥራታቸው በበርካታ ሙዚቀኞች ዘንድ ተወዳጆች ናቸው፤ ዝነኞቹን የአርጀንቲናው ጊታር ተጫዋች ጆርግ ሞሬል (Jorg Morel) እና ስፔናዊው ፓኮ ደ ሉቺያን (Paco De Lucia) ጨምሮ።
እ.አ.አ ከ2008 ዓ.ም በፊት ሉቲየር (Luthier) በተባለው የሙዚቃ መሳሪያ አቅራቢ ኮርፖሬሽን በከፍተኛ ደረጃ ሽያጭ ታዋቂ ነበሩ የቶኒ የጊታር ክር ምርቶች። የሽያጭ ገቢው ብቻ በአመት እስከ 2.5 ሚልየን ዶላርስ ደርሶ ነበር። በዚያን ጊዜ ከናይሎን የተሰራ የጊታር ክር ነበር የሚያመርተው፤ የተለየ የድምፅ ቃና እና ለተጫዋቹ ምቾት የሚሰጥ በመሆኑም ተመራጭ ነበር።
በዩናይትድ ስቴትስ የምጣኔ ሃብት ባዘቀዘቀበት አመታቶችና ገበያ በጠፋበት ጊዜ ቶኒ አኮስታ የማከፋፈያ መደብሮቹን እስከመሸጥ ደርሶ ነበር።
ሰላሳ አመታትን ያስቆጠረው የቶኒ የጊታር ክር ምርት በድጋሚ በብዛትና በጥራት ገበያውን ተቆጣጥሮታል። ድርጅቱ በብዛትና በስፋት ማምረት ይችላል፤ ነገር ግን በአንድ ጊዜ ብዙ ማምረትን አይፈልግም ቶኒ እንዳለው ።
“ምርቱ በጥራት እስከተሰራ ድረስ ገንዘብ ይመጣል። ትክክለኛ ድምፅና ቃና የሚሰጠውን የጊታር ክር መስራት መቻል ነው የሚያስጨንቀኝ፣ ተመራጭ ለመሆን ደግሞ የግል ችሎታና ተሰጦን ይጠይቃል” ብሏል ቶኒ።
የቪኦኤው ባልደረባችን ራሞን ታይሎርን (Ramon Taylor) ዘገባ መስታወት አራጋው ታቀርበዋለች። ሙሉ ዝግጅቱን ከበታች ያለውን የድምፅ ምልክት በመጫን ያዳምጡ።