ኢትዮጵያ በቅርቡ የምታደርገውን ምርጫ ለመከታተል ከዓለም አቀፍ እንዲሁም ሀገራዊ ተቋማት የተውጣጡ ታዛቢዎች ኃላፈነታቸውን ለመወጣት ዝግጅታቸውን እየጨረሱ መሆናቸውን የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ።
የሚኒስቴሩ ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲን የጠቀሰው ማብራሪያ የአውሮፓ ህብረት የምርጫ ታዛቢዎችን የመላክ ዕቅዱን ቢሠርዝም የባለሙያዎች ልኡክ ለመላክ መወሰኑ ተገልጿል።
የምርጫ ታዛቢዎች ተገቢነት ባለው የኢትዮጵያ ተቋም የተቀመጡ ህግ እና ደንቦችን ያከብራሉ ተብሎ እንደሚጠበቅም ተገልጿል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የሀገሪቱ ም/ ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ከዮናይትድ ስቴትስ መንግሥት የአፍሪካ ቀንድ ልዩ ልዑክ ጄፍሪ ፌልትማን ጋር መወያየታቸው ተሰምቷል።
ውይይታቸው በትግራይን ክልል ወቅታዊ የሰብዓዊ ድጋፍ እና የመልሶ ማቋቋም እንቅስቃሴዎች፣ የኢትዮ ሱዳን ድንበር ጉዳይ እና የኅዳሴ ግድብ ድርድር ላይ ያተኮረ እንደነበረ ተገልጿል።
ሁለቱ ባለሥልጣናት በውይይታቸው የውሃ ሙሌት እና እና ከሱዳን ጋር ያለው የድንብር ውዝግብ በሰላማዊ መንገድ ሊፈታ እንደሚገባ አጽንኦት ሰጥዋል ብሏል ሚኒስቴሩ በማስገንዘቢያው።
በሁለቱ ሀገራት መካከል የቆየውን የረጅም ጊዜ ግንኙነት ማጎልበት ስለሚኖረው ጠቃሜታም ማውሳታቸው ተጠቅሷል።