በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ዓለም አቀፍ የእርዳታ ሰጭ ድርጅቶች - በትግራይ ክልል


ፎቶ ፋይል፦ መቀሌ
ፎቶ ፋይል፦ መቀሌ

በትግራይ ክልል 135 ዓለም አቀፍ እርዳታ ሰጪ ድርጅቶች የተሰማሩ ቢሆንም የሚያደርጉት ድጋፍ አነስተኛ ነው ሲል የጊዜያዊ አስተዳደሩ የመንግሥት ኮምኒኬሽን ቢሮ ገለጸ።

የቢሮው ሃላፊ ወይዘሮ እቴነሽ ንጉሤ ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት የትግርኛ ወጋሕታ ጋዜጣ በሰጡት ቃል፤ የተወሰኑ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች አልሚ ምግቦችንና ምግብ ነክ ያልሆኑ ቁሳቁስ እያበረከቱ ቢሆንም ከእነሱ ከሚጠበቀው አንጻር ዝቅተኛ ነው ብለዋል።

አያይዘውም ቃል አቀባይዋ የዓለም የምግብ ፕሮግራም እና ቀይ መስቀል የመሳሰሉ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች እገዛ እያደረጉ ቢሆንም፤ በክልሉ ከገቡት እርዳታ ሰጪ ድርጅቶች ቁጥርና ከደረሰው ጉዳት አንፃር ሲታይ አሁን ካለው ድጋፋቸው በላይ እርዳታ መስጠት ይጠበቅባቸው ነበር ብለዋል፡፡

መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች እርዳታ በማከፋፋል ሂደት የሚጋጥሙ ችግሮችን በመፍታት በቀጣይ ህፃናት ላይ ትኩረት በማድረግ አልሚ ምግብ እንዲሰጡ ቃል ገብተዋል ያሉት ወይዘሮ እቴነሽ፤ ቃላቸውን ይጠብቃሉ ብለን ተስፋ እናደርጋለን ብለዋል፡፡

በአሁኑ ሰአት ያሉት ተፈናቃዮች የሚስፈልጋቸው አስቸኳይ እርዳታ በቀጥታ ሊመገቡት የሚችሉትን የተዘጋጁ ምግቦችን እንደሆነ ጠቅሰው፤ መንግሥት ለተፈናቃዮቹ ከሚሰጥው መጠለያ በተጨማሪ በሃገር ውስጥ እና በውጭ ያሉት የክልሉ ተወላጆች እና ባጠቃላይ ኢትዮጵያውያን እገዛ እንዲያረጉ ጠይቀዋል፡፡

የትግራይ ክልል ሰብአዊ ድጋፍ 70 በመቶ በመንግሥት እየተሸፈነ ሲሆን፤ ከ135 በላይ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች በክልሉ እርዳታ ለመስጠት ቢገቡም የሚሰሩት ስራ በቂ እንዳልሆነ እና መንግሥት ብቻውን ለ4 ነጥብ 2ሚሊዮን ዜጎች ሰብዓዊ እርዳታ ማቅረቡን የጋዜጣው ዘገባ አክሎ አመልክቷል።

XS
SM
MD
LG