የመካከለኛው ምስራቅና የሰሜን አፍሪካ አገራት በጦርነት፣ በፖለቲካ አለመረጋጋትና በኢኮኖሚያዊ ችግሮች ሲታመሱ ኖረዋል። ኮቪድ 19 ደግሞ ችግሮቹን የበለጠ እያባባሳቸው ነው።
የተባበሩት መንግስታት ድርጅቶች ያልተረጋጉና ጠንክረው ያልወጡ መንግስታት ያሏቸው እነዚህ አገራት ወረርሽኙንና ከወረርሽኙ ጋር የሚመጡ ተያያዥ ችግሮችን ለመቋቋም የሚያስችል አቅም የላቸውም ሲሉ ያስጠነቅቃሉ። የዓለም ምግብ ድርጅት የምግብ ቀውስን አስመልክቶ ባወጣው ሪፖርት በዓለማችን ላይ በምግብ እጥረት ከሚሰቃዩ ህዝቦች 20 በመቶ የሚሆኑት በመካከለኛው ምስራቅ እንደሚገኙ አመልክቷል።
የምግብ ድርጅቱ የሕዝብ ግንኙነት ሀላፊ ኤሊዛቤጥ ባየርስ፣ ወረርሽኙ ረሀቡን ወደ ከፋ ደረጃ እንደሚያደርሰውና ሰዎች መተዳደሪያ ምንጫቸውን እያጡ በሄዱ ቁጥር ራሳቸውን መመገብ እንደሚያቅታቸው ይገልፃሉ።
በአሁኑ ውቅት የዓለም ምግብ ድርጅት በአካባቢው ላሉ 23 ሚሊዮን ሰዎች ምግብ ያቀርባል። ከዚህ ውስጥ ሁለት ሦስተኛው የሚሆነው በጦርነት፣ በበሽታና በረሀብ ለሚሰቃዩት የየመንና ሶሪያ ሕዝቦች የሚላክ ነው።
(ዘገባውን በድምፅ ለማድመጥ የተያያዘውን የድምፅ ፋይል ይጫኑ)