የኢትዮጵያና የሶማሊያ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትሮች ሁለተኛ ዙር ውይይት ሊያደርጉ ነው

ፎቶ ፋይል፦ የቱርክ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ሃካን ፊዳን

Your browser doesn’t support HTML5

የኢትዮጵያና የሶማሊያ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትሮች ሁለተኛ ዙር ውይይት ሊያደርጉ ነው

ኢትዮጵያ ከሶማሊላንድ ጋራ የፈረመችው የባሕር በር አጠቃቀም ስምምነት የፈጠረውን አለመግባባት በተመለከተ፣ የኢትዮጵያና የሶማሊያ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር በሚቀጥለው ሳምንት አንካራ ላይ ተገናኝተው ለሁለተኛ ዙር እንደሚወያዩ የቱርክ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ሃካን ፊዳን ዛሬ ዓርብ አስታወቀዋል።

ታኅሳስ 22 ቀን 2016 ዓ.ም ፣ ወይም በያዝነው የፈረንጆች ዓመት በመጀመሪያው ቀን፣ ኢትዮጵያ 20 ኪ/ሜ የሚደርስ የባሕር ዳርቻ ከሶማሊላንድ በሊዝ ለመያዝ ስምምነት መፈራረሟ፣ ሶማሊላንድን እንደራሷ ግዛት ከምትቆጥራት ሶማሊያ ጋራ ቅራኔ ውስጥ ከቷታል። ኢትዮጵያ ይህን ችሮታ ለመመለስም ከሶማሊያ ተገንጥላ ራሷን ለምታስተዳድረው ሶማሊላንድ ነጻ ሃገር ስለመሆኗ እውቅና ለመስጠት ተስማምታ ነበር ተብሏል።

ሞቃዲሹ ስምምነቱን ሕገ ወጥ ነው በማለት፣ በሃገሪቱ ይገኙ የነበሩትን የኢትዮጵያ አምባሳደር እንዲወጡ አድርጋለች፡፡ በዛች ሃገር ከእስላማዊ አማጺያን ጋራ ለሚደረገው ፍልሚያ እገዛ በማድረግ ላይ ያሉትን የኢትዮጵያ ወታደሮችንም ለማስወጣት ዝታለች፡፡

SEE ALSO: ቱርክ ሶማሊያ እና ኢትዮጵያ በወደብ ስምምነቱ ዙሪያ የሚያደርጉትን ውይይት እያደራደረች ነው

የሶማሊያ እና የኢትዮጵያ የውጪ ጉዳይ ምኒስትሮች በፊዳን አስተናጋጅነት ባለፈው ወር አንካራ ላይ ለመጀመሪያው ዙር ውይይት ተገናኝተው ነበር።

ባለፈው ቅዳሜ አዲስ አበባ ላይ ከኢትዮጵያው ጠቅላይ ምኒስትር ዐብይ አህመድ ጋራ ተገናኝተው የነበሩት የቱርኩ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ሃካን ፊዳን፣ ሁለተኛው ዙር ውይይት በመጪው ሳምንት እንደሚካሄድ ዛሬ ኢስታንቡል ላይ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቀዋል።

ከጠቅላይ ምኒስትር ዐብይ አህመድ ጋራ በዝርዝር ጉዳዮች ላይ እንደተነጋገሩ የገለጹት ፊዳን፣ “ኢትዮጵያ የሶማሊያን የድንበር እና የፖለቲካ ሉአላዊነት እስካከበረች ድረስ፣ በሶማሊያ በኩል የባሕር በር ተጠቃሚ ትሆናለች፣ ይህም በኢትዮጵያ እና በሶማሊያ መካከል ያለውን ውጥረት መፍትሄ ይሰጣል” ብለዋል።

SEE ALSO: ኢትዮጵያና ሶማሌላንድ የባሕር በር ውል ቋጠሩ

ቱርክ የሶማሊያ መንግሥት የቅርብ አጋር ሆናለች። ትምህርት ቤቶችን፣ ሆስፒታሎችን፣ ወታደራዊ ሠፈሮችን እና ሌሎችንም መሠረተ ልማቶች ገንብታለች፡፡ ከሰባት ዓመታት በፊትም ሁለቱ ሃገራት የወታደራዊ እና የኢኮኖሚ ትብብሮችን ተፈራርመዋል።