በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

የቦምብ ጥቃት ዛቻ የደረሳቸው የዚምባቡዌ ፕሬዚዳንት በረራቸውን አቋረጡ


የዚምባቡዌ ፕሬዝዳንት ኤምርሰን ምናንጋግዋ
የዚምባቡዌ ፕሬዝዳንት ኤምርሰን ምናንጋግዋ

በአንድ ዓለም አቀፍ ጉባኤ ላይ ላይ ለመሳተፍ ዛሬ ዓርብ ወደ ቪክቶሪያ ፎልስ ከተማ በአውሮፕላን እየተጓዙ የነበሩት የዚምባቡዌ ፕሬዝዳንት ኤምርሰን ምናንጋግዋ በረራቸውን አቋርጠው ከመዳረሻቸው ሳያርፉ ተመለሱ፡፡

ፕሬዚዳንቱ ጉዟቸውን ያቋረጡት ባለሥልጣናት ከተረጋገጠ ምንጭ የቦምብ ጥቃት እንደሚካሄድባቸው የሚገልጽ ኢሜል ከደረሳቸው በኋላ ነው፡፡

የፕሬዚዳንቱ ቃል አቀባይ ጆርጅ ቻራምባ ዛሬ በሰጡት መግለጫ እንደተናገሩት ፕሬዚዳንቱ ቪክቶሪያ አውሮፕላን ማረፊያ እንደደረሱ የቦምብ ጥቃት እንደሚጠብቃቸው የሚገልጽ ኢሜል የደረሳቸው መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡

ለጥንቃቄ ሲባል የሀገሪቱ ደህንነት በአሁኑ ወቅት በከፍተኛ ደረጃ ተጠንቀቅ ላይ እንዲሆን መደረጉን ቃል አቀባዩ ገልጸዋል፡፡

የሥጋቱ ምንጭ እየተጣራ እንደሚገኝና ሲጠናቀቅ ይፋ እንደሚደረግ አስታውቀው እስከዚያው ድረስ ህዝቡ እንዲረጋጋ ቃል አቀባዩ በመግለጫቸው አሳስበዋል፡፡

በርካታ ዓለም አቀፍ ጉባኤዎች የሚካሄዱባት የቪክቶሪያ ከተማ የዚምባብዌ ዋነኛዪቱ የቱሪስት መዳረሻ ስትሆን ሀገሪቱን ከዛምቢያ ጋር በሚያዋስነው ድንበር አጠገብ ከሐራሬ በ900 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የምትገኝ ከተማ ናት፡፡ ፡

ፕሬዝዳንት ምናንጋግዋ ሲያመሩ የነበረው የደቡብ አፍሪካ ሀገሮች ዓለም አቀፍ የታዳሽ ኃይል ጉባኤ የመዝጊያ ስነስርዓት ላይ ለመገኘት ነበር፡፡

መድረክ / ፎረም

XS
SM
MD
LG