በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

"ሶማሊያ ላይ የተደቀነውን ከባድ ቸነፈር የለጋሾች መጠነ ሰፊ ድጋፍ ሊያዘገየው ችሏል" የዓለም ምግብ ፕሮግራም


ፎቶ ፋይል፦ የሶማሊያ ተፈናቃዮች በዶሎ፣ ሶማሊያ 09/ 19/2022
ፎቶ ፋይል፦ የሶማሊያ ተፈናቃዮች በዶሎ፣ ሶማሊያ 09/ 19/2022

"ዩናይትድ ስቴትስ እና ጀርመንን ከመሳሰሉ ለጋሾች በተገኘው ድጋፍ ሶማሊያ ላይ የተደቀነው የቸነፈር አደጋ ሙሉ በሙሉ ተቀልብሷል ባንልም አዘግይቶታል" ሲሉ የዓለም የምግብ ፕሮግራም ዋና ሥራ አስኪያጅ ተናገሩ። አደጋው ተወግዷል ማለት አለመሆኑን አጥብቀው ሳያስገነዝቡ አላለፉም።

የኖቤል የሰላም ሽልማት ተሸላሚው ዴቪድ ቢዝሊ ይህን ያሉት ስዊዘርላንድ ዳቮስ እየተካሄደ ባለው የዓለም የኢኮኖሚ ጉባዔ ላይ ለአሶሲየትድ ፕሬስ በሰጡት ቃል ነው።

የአፍሪካ ቀንድ ሀገሮች ለጋሾች ለዓመታት ባጠቃቸው ድርቅ ታይቶ የማይታወቅ ከባድ ጉዳት አድርሶባቸዋል ብለው "ለጋሾች ድንቅ በሆነ መንገድ ባይታደጉ ኖሮ ሶማሊያ ውስጥ ከባድ ቸነፈር ገብቷል ብለን ለማወጅ ተዘጋጅተን ነበር" ብለዋል።

በመጪው ሚያዚያ ስራቸውን ለመልቀቅ ያቀዱት የቀድሞው ሪፐብሊካን የደቡብ ካሮላይና አገረ ገዢው ዴቪድ ቢዝሊ የፖለቲካ መስክ ያካበቱትን ተሞክሮ በመጠቀም ከባይደን አስተዳደር እና በፊትም ከትረምፕ አስተዳደር ለዓለም የምግብ ፕሮግራም መጠነ ሰፊ ድጋፍ ለማግኘት እንደቻሉ ይነገርላቸዋል።

ባለፈው ወር የተመድ እና ሌሎች አካላት ባወጡት ሪፖርት 8 ሚሊዮን ሶማሊያውያን በአስከፊ የምግብ ዋስትና ችግር ላይ እንዳሉ ማስታወቃቸውን ተከትሎ ዩናይትድ ስቴትስ 411 ሚሊዮን ዶላር ለግሳለች።

ቢዝሊ እአአ በ2017 ዋና ሥራ አስኪያጅነቱን ሲይዙ በዓለም ዙሪያ የምግብ ዋስትና ዕጦት ላይ የነበሩት ሰዎች ቁጥር 80 ሚሊዮን እንደነበር ያወሳው የአሶስየትድ ፕሬስ ዘገባው አሁን በግጭት በአየር ንብረት ለውጥ እና በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ሳቢያ በተፈጠረው የኢኮኖሚ መቆርቆዝ እና የምግብ አቅርቦት ሰንሰለት መቆራረጥ 350 ሚሊዮን መድረሱን አመልክቷል።

XS
SM
MD
LG