ዋሽንግተን ዲሲ —
የዩናይትድ ስቴትስ ከፍተኛ ባለሥልጣናት፣ ከዛሬ ቅዳሜ ጀምሮ፣ ዩናይትድ ስቴትስ አፍጋኒስታንን ለቃ ከወጣች ወዲህ፣ ለመጀመሪያ ጊዜ፣ አፍጋኒስታንን ከሚያስተዳደሩት የታሊባን ተወካዮች ጋር ፣ በአካል ተገናኝተው እንደሚነጋገሩ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባለሥልጣናት አስታወቁ፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባለሥልጣናቱ፣ ዛሬ ቅዳሜና ነገ እሁድ በኳታር ዶኻ፣ ከታሊባን ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጋር ተገናኝተው እንደሚነጋገሩ አስታውቀዋል፡፡፡
የንግግሩን ዜና ለመጀመሪያ ጊዜ የናኘው ሮይተርስ፣ ንግግሩ ላይ በዩናይትድ ስቴትስ በኩል፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባለሥልጣናት፣ የዓለም አቀፍ ልማትና እርዳታ፣ እንዲሁም የመረጃ ማህበረሰብ አባላት እንደሚገኙበት አመልክቷል፡፡
የታሊባን ከፍተኛ ባለሥልጣናትም፣ በተባለው ቦታና ቀናት እንደሚገኙም፣ የታሊባን ከፍተኛ ባለሥልጣን ሱሃሂል ሻኺን ለቪኦኤ አረጋግጠዋል፡፡
ንግግሩ፣ በታሊባን የቀሩት አሜሪካውያን ዜጎችና ፣ ተባባሪዎቹ የአፍጋን ዜጎች፣ ከአገር የሚወጡበትን መንገድ ጨምሮ፣ አፍጋኒስታን ባለችበት ወቅታዊ ጉዳይና፣ በሁለቱ አገሮች መካከል ስለሚኖረው ግንኙነት እንደሚሆን ተገልጿል፡፡