ዋሺንግተን ዲሲ —
ሁለት የዩናይትድ ስቴትስ የምክር ቤት አባላት ቀደም ሲል ባልተገልጸ የጉዞ መርሃ ግብር ወደ አፍጋኒስታን ዋና ከተማ ካቡል መጓዘቸው ተገለጸ፡፡
የምክር ቤቱ አባላት ከጉዟቸው መልስ ትናንት ማክሰኞ በሰጡት መግለጫ እንዳስታወቁት፣ የጉዟቸው ዓላማ ዜጎችን ካገር የማስወጣቱ ሂደት ያለበትን ሁኔታ ለመገምገም፣ እንዲሁም፣ የአሜሪካ ወታደሮች፣ ከአፍጋኒስታን ተጠናቀው እንዲወጡ እኤአ ነሀሴ 31 የተያዘው ቀነ ገደብ እንዲራዘም፣ በፕሬዚዳንት ጆ ባይደን ላይ ግፊት ለማድረግ መሆኑ ተነግሯል፡፡
በምክር ቤቱ የወታደራዊ ጉዳዮች ኮሚቴ አባላት፣ የማሳቹሴትስ ዴሞክራት ሴት ሞልተን እና የሚችጋኑ ተወካይ ፒተር ሚጀር፣ ከጉዟቸው በኋላ፣ ዛሬ በሰጡት መግለጫ “ሁኔታውን እንደተመለክትነው በተባለው ጊዜ ውስጥ ሁሉንም ሰው ማውጣት አንችልም “ብለዋል፡፡
ፕሬዚዳንት ባይደን፣ ትናንት በሰጡት መግለጫየማስወጣቱ ሥራ በዚህ ወር መጨረሻ ላይ ይጠናቀቃል ብለዋል፡፡
ዋይት ሀውስም በዛሬ ጧት ማብራሪያው በ24 ሰዐት ጊዜ ውስጥ፣ 19ሺ ሰዎችን ማውጣት መቻሉን አስታውቋል፡፡
ከነሀሴ አጋማሽ ጀምሮ እስካሁን የወጡት ሰዎች ቁጥር 82ሺ መድረሳቸውም ተመልክቷል፡፡