ዋሽንግተን ዲሲ —
የባይደን አስተዳደር ዩናይትድ ስቴትት እኤአ በ2022 በሚደረገው የቤጂንግ የክረምት ኦሎምፒክ ጨዋታዎች ላይ፣ የዲፕሎማሲ ተአቅቦ በማድረግ፣ ከዩናይትድ ስቴትስ የአትሌቲክስ ቡድን በስተቀር የትኛውም የዩናይትድ ስቴትስ ባለሥልጣን የማይሳተፍ መሆኑን፣ በዚህ ሳምንት ታሳውቃለች ተብሎ እንደሚጠበቅ የዩናይትድ ስቴትስ ዜና ማሰራጫዎች ዘገቡ፡፡
ዜናውን መጀመሪያው የዘገበው ሲኤንኤን ነው፡፡
አትሌቶቹን ሳይጨምር የዲፕሎማሲው መገለል የተወሰነው እኤአ በ1980 በፕሬዚዳንት ጂሚ ካርተር ዘመን ሶቭየት ህብረት አፍጋኒስታንን ወራለች በሚል ዩናይትድ ስቴትስ አትሌቶቿን ከሞስኮው የበጋ ኦሎሞፒክ በማገድ የፈጸመችውን ስህተት ላለመድገም መሆኑ ተገልጿል፡፡
ቻይና በሚሊዮን በሚቆጠሩ ሙስሊም ቻይናውያንን አስራለች፣ በሆንግ ኮንጎ የዲሞክራሲ ኃይሎችን ታጠቃለች የሚለውን ጨምሮ፣ ትፈጽማዋለች በሚባለው የሰብአዊ መብት ጥሰት፣ ፕሬዚዳንት ባይደን እርምጃዎችን እንዲወስዱ፣ በህግ አውጭ የምክር ቤት አባላት፣ ከፍተኛ ግፊት እየደረሰባቸው መሆኑ በዘገባው ተጠቅሷል፡፡
ባይደን ባለፈው ወር እኤአ የካቲት 4 እስከ 20 በሚደረገው የቻይናው የክረምት ኦሎምፒክ የዲፕሎማሲ ተአቅቦ እንደሚያደርጉ አስታውቀው ነበር፡፡