በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ዩናይትድ ስቴትስ ኃይሎች በኢራን በሚደገፉ ሚሊሻዎች ላይ የአጸፋ ጥቃት ፈጸሙ


ፎቶ ፋይል፦ የሂዝቦላህ ተዋጊዎች ወታደራዊ ታንክ አጠገብ እየተጓዙ በበምዕራባዊ ቃላሞን፣ ሶሪያ፣ እአአ ነሃሴ 23/2017
ፎቶ ፋይል፦ የሂዝቦላህ ተዋጊዎች ወታደራዊ ታንክ አጠገብ እየተጓዙ በበምዕራባዊ ቃላሞን፣ ሶሪያ፣ እአአ ነሃሴ 23/2017

የዩናይትድ ስቴትስ ኃይሎች ኢራቅ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ በኢራን የሚደገፉ ሚሊሻዎችን ዒላማ ያደረገ ጥቃት ትናንት ሰኞ ፈጽመዋል፡፡

ጥቃቱ የተፈጸመው ሚሊሻዎቹ በሦስት የዩናይትድ ስቴትስ ወታደሮች ላይ ጉዳት በማድረስ ለፈጸሙት የሰው አልባ አውሮፕላን ጥቃት የተሰጠ ምላሽ መሆኑ ተመልክቷል፡፡

የዩናይትድ ስቴትስ ጥቃቱን የፈጸመችው በካታብ ሂዝቦላህ እና ተባባሪ ቡድኖች በሚጠቀሙባቸው ሦስት ቦታዎች ላይ መሆኑን የመከላከያ ሚኒስትር ሎይድ ኦስቲን ባወጡት መግለጫ አስታውቀዋል።

ሚኒስትሩ በመግለጫቸው "እነዚህ ትክክለኛ ጥቃቶች በኢራን የሚደገፉ ታጣቂዎች በኢራን እና በሶሪያ በአሜሪካ ወታደሮች ላይ ለተሰነዘረው ተከታታይ ጥቃት ምላሽ ናቸው፣” ብለዋል፡፡

”ይህ ጥቃት በኤርቢል የአየር ኃይል ጦር ሠፈር ላይ ያደረሱትን ጥቃት ጨምሮ፣ ለጥቃቱ በቀጥታ ተጠያቂ የሆኑትን የኢራን ተባባሪ የሆነውን ካታይብ ሄዝቦላህ እና የተባባሪ ቡድኖችን አቅም ለማዳከምና ለማሽመድመድ ታስቦ ነው። ሲልም የሚኒስትሩ መግለጫ ጨምሮ አመልክቷል፡፡

የብሔራዊ ደኅንነት ምክር ቤት ቃል አቀባይ አድሪያን ዋትሰን እንዳስታወቁት ካታይብ ሂዝቦላህ በኢራን የሚደገፉ ታጣቂዎች አቃፊ ቡድን በመሆን ሰኞ ለደረሰው ጥቃት ኃላፊነቱን መውሰዱን አስታውቀዋል፡፡

በጥቃቱ አንድ የዩናይትድ ስቴትስ ወታደር በጽኑ መቁሰሉንም ቃል አቀባዩ ገልጸዋል፡፡

የኢራቅ መንግሥት የዩናይትድ ስቴትስ የአየር ጥቃቶችን የተቃወመ ሲሆን "የጠላት ድርጊት" እና የኢራቅን ሉዓላዊነት የጣሰ ነው ብሏል፡፡

በኢራቅእና ሶሪያ የሚገኘውን የእስላማዊ መንግሥት ቡድንን ለመመከት የናይትድ ስቴትስ እና ጥምር ኃይሎች በክልሉ ውስጥ መንቀሳቀሳቸው ተመልክቷል፡፡

እነዚያ ኃይሎች በኢራን በሚደገፉ ወኪሎች ተደጋጋሚ ጥቃቶች ሲደርሱባቸው እስራኤል በጋዛ ሰርጥ የሚገኘውን ሐማስ የተባለውን ታጣቂ ቡድን ለማጥፋት ጥቃት ከጀመረች ወዲህ ወደ 100 የሚጠጉ ጥቃቶች የደረሱባቸው መሆኑ ተመልክቷል፡፡

የዩናይትድ ስቴትስ ጦር አብዛኞቹን ጥቃቶች እንዳመከኑ ወይም ዒላማቸውን ስተው በመውደቃቸው ምንም ጉዳት አላደረሱም ብሏል።

ይሁን እንጂ ባለፈው ሰኞ የነበሩት ዓይነት አብዛኞች ጥቃቶች የዩናይትድ ስቴትስ የጦር አባላት ላይ ጉዳት ማድረሳቸው ተመልክቷል፡፡

የዩናይትድ ስቴትስ በህዳር ወር የፈጸመቻቸውን ጥቃቶች ጨምሮ ከዚህ ቀደም የተፈጸሙ የአጸፋ ጥቃቶች በካታብ፣ ሂዝቦላህ እና በሌሎች ቡድኖች ላይ ያነጣጠሩ እንደነበር ተገልጿል፡፡

መድረክ / ፎረም

XS
SM
MD
LG