በደቡባዊ ኒው ሜክሲኮ ግዛት በሚገኘው 'ሩዶሶ' ከተማ ውስጥ በከፍተኛ ሁኔታ እየተዛመተ በሚገኘው ፈጣን ሰደድ እሳት ምክንያት ነዋሪዎች ምንም አይነት ንብረታቸውን ማንሳት ሳይችሉ ቤታቸውን ለቀው እንዲወጡ ታዘዋል።
7 ሺህ ሰዎች የሚኖሩበት መንደር ነዋሪዎች አካባቢያቸውን ጥለው እንዲወጡ የተነገራቸው ሰኞ እለት ከምሽቱ አንድ ሰዓት አካባቢ ነው።
የኒው ሜክሲክኮ ግዛት የሕዝብ አገልግሎት ሰጪ ተቋም በእሳቱ ምክንያት የመንደሩን የተወሰነ ክፍል የኤሌክትሪክ አገልግሎት አቋርጧል። ተቋሙ በርካታ መዋቅሮች ስጋት ላይ መሆናቸውን እና የተወሰኑት መውደማቸውን ያስታወቀ ሲሆን ከመንደሩ በስተደቡብ የሚገኘው የዩናይትድ ስቴትስ አውራ ጎዳና ዝግ ሆኗል።
ማስጠንቀቂያው ሲደርሳቸው ቤተሰቡ ምግብ ለመብላት እየተዘጋጀ እንደነበር ለኬኦቢ ቴሌቭዥን ጣቢያ የተናገረችው ሜሪ ሉ ሚኒክ፣ "አሁኑኑ ለቃችሁ ውጡ። ምንም ነገር ለመያዝ አትሞክሩ። ዝም ብላችሁ ውጡ" የሚል መልዕክት እንደደረሳቸው እና ከአምስት ደቂቃ ባነሰ ጊዜ ውስጥ መኪና ውስጥ ገብተው መንገድ መጀመራቸውን አስረድታለች።
'ሜስካሌሮ አፓቺ' ከተሰኘው ጥብቅ ቦታ ቀደም ብሎ የተነሳው እሳት ወደ 8.2 ስኩዌር ማይልስ ማደጉን እና እስካሁን በምንም መልኩ መቆጣጠር እንዳልተቻለ የግዛቱ የደን ባለስልጣናት ተናግረዋል። ከሩዶሶ በስተደቡብ ምዕራብ የተነሳው ሁለተኛው የእሳት ቃጠሎ ደግሞ 4.3 ስኩዌር ማይልስ የሸፈነ ነው። ከመንደሩ 75 ማይል ርቀት ላይ በሚገኘው ሮዝዌል ከተማ በርካታ የመጠለያ ማዕከላት ተዘጋጅተዋል።
ሰደድ እሳቱ ባስከተለው ጭስ ምክንያት ሩዱሶ መንደር እና አካባቢው ጤናማ ባልሆነ አየር መበከሉን የሚገልጽ የአየር ጥራት ማስጠንቀቂያም ለነዋሪዎች ተሰጥቷል።
መድረክ / ፎረም