በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ኮቪድ-19 በሶማሊያ


ፎቶ ፋይል፦ የኮቪድ ታማሚዎች ሶማሊያ፣ ሞቃዲሾ ማገገሚያ ሆስፒታል።
ፎቶ ፋይል፦ የኮቪድ ታማሚዎች ሶማሊያ፣ ሞቃዲሾ ማገገሚያ ሆስፒታል።

ሶማሊያ ውስጥ በኮቪድ የሞተው ሰው ብዛት በይፋ ከተነገረው በጣም ከፍ ያለ መሆኑን አንድ ጥናት አመለከተ።

ሶማሊያ ውስጥ በኮቪድ-19 ወረርሽኙ የመጀመሪያ ወራት በኮቪድ ምክንያት ህይወታቸው ያለፈው ሰዎች ቁጥር የሀገሪቱ መንግሥት ካለው ቢያንስ በሰላሳ ሁለት ከመቶ ይበልጣል ሲል አንድ አዲስ ጥናት አመለከተ።

ዓለም አቀፍ የተላላፊ በሽታዎች መጽሄት ላይ የታተመው ጥናት እንደሚለው በሶማሊያ ዋና ከተማ ሞቃዲሾ ውስጥ እአአ ባለፈው 202 ከመጋቢት እስከ መስከረም በነበሩት ወራት ውስጥ በኮቪድ ሳቢያ የሞቱት ሰዎች ቁጥር በትንሹ ከ3200 እስከ 11800 ይሆናል ተብሎ እንደሚገመት ገልጿል።

በዚያ ጊዜ ውስጥ የሶማሊያ መንግሥት በኮቪድ ምክንያት ሞተዋል ብሎ ሪፖርት ያደረገው ዘጠና ዘጠኝ ሰዎች በሀገሪቱ ባጠቃላይ በቫይረሱ ተይዘዋል ብሎ ያወጣው አሃዝ ደግሞ 21,269 መሆኑን ይህ አዲስ ጥናት ዘርዝሯል። የጥናቱ ተመራማሪዎች ይህ በተጨባጭ ካለው የቫይረሱ ተጋላጮች ቁጥር እጅግ ያነሰ መሆኑን ነው የገለጹት።

በለንደን የሃይጂንና የቆላማ አካባቢዎች ተላላፊ በሽታዎች ትምህርት ቤት በተካሄደው ጥናት ከተካፈሉ ተመራማሪዎች አንዱ የሆኑት አብደልሃሚድ ዋርሳሜ "ሶማሊያ ዕድለኛ ሆና ብዙ ሰው አልታመመባትም፣ አልሞተባትም ማለት አይበቃም" ብለዋል። የሞቱት ሰዎች ቁጥር ለመጨመሩ ምክንያት ሊሆን የሚችል ሌላ ወረርሽኝም ይሁን የተፈጠረ አደጋ አላየንም ሲሉም ተመራማሪው አክለው አስረድተዋል።

ተመራማሪዎቹ ከድምዳሜያቸው የደረሱት እአአ ከ2016 ጀምሮ እስከ 2020 ዓመተ ምህረት የቀብር ስፍራዎችን በሳተላይት አማካይነት የተቀረጹ መቃብሮችን የሚያሳዩምስሎች በማጥናት፤ ነዋሪዎችን በማነጋገር እንዲሁም በአገሪቱ ያሉ ተጨባጭ አሃዛዊ መረጃዎችን በመገምገም መሆኑን ነው ያስታወቁት። አዲሱን ጥናት ያልተቀበሉም አሉ።

በሶማሊያ የዓለም የጤና ድርጅት ተጠሪ ዶክተር ማሙኑር ራህማን ማሊክ ግን ጥናቱ ትክክለኝነት ይጎድለዋል ይላሉ።

የዓለም የጤና ድርጅቱ ተጠሪ ለቪኦኤ የሶማሊኛ ክፍል በሰጡት ቃል "ቁጥሩ ይሁን በሳይንሳዊ መንገድ የተቀመረ አሃዝ ነው ነገር ግን በሀገሪቱ በኮቪድ ምክንያት የሞቱትን ሰዎች ብዛት በርግጠኝነት የሚያንጸባርቅ ሊሆን አይችልም። ምናልባት ትክክለኛው አሃዝ መንግሥት በሰጠው ዝቅተኛ ቁጥር እና በዚህ ጥናት በቀረበው አሃዝ መሃል ሊሆን ይችላል" ብለዋል።

የለንደን ስኩል ትሮፒካል ሜዲሲን ተመራማሪው ዋርሳሜ ሲያስረዱ ባለፈው ዓመት ከመጋቢት እስከ መስከረም በነበሩት ወራት የታዩት አዲስ መቃብሮች በሙሉ በቀጥታ በኮቪድ ምክንያት የሞቱ ሰዎችን ቁጥር የሚያሳዩ ናቸው ማለታችን ሳይሆን ወረርሺኙ በህበረተሰቡ ላይ ባስከተለው ጫና የተነሳ የጠፋውን ህይወትም ይጨመራል ብለዋል።

"የኮቪድ ስርጭት በበረታበት ወቅት የሀገሪቱ የጤና አገልግሎት ተዳክሟል። የሌሎች ክትባቶች እንቅስቃሴ እንዲሁም የእናቶች እና ህጻናት ጤና አገልግሎት ቀንሷል ስለዚህ እሱም ለሞት አሃዙ መጨመር ምክንያት ሊሆን ይችላል። በመሆኑም በሞት ቁጥሩ መጨመር ላይ ኮቪድ-19 በቀጥታ እና በተዘዋዋሪ ያስከተለው ውጤት ተብሎ ሊወሰድ ይችላል" ብለዋል።

መንግሥት በኮቪድ-19 ምክንያት ሞቱ ብሎ የሚያወጣው አሃዝ በጤና ተቋማት ውስጥ የሚሞቱትን ብቻ መሆኑን ያመለከቱት አጥኚው ሌላውን ከህክምና ተቋማት ውጭ በበሽታው ሳቢያ የሚሞቱትን ሰዎች ቁጥር ለመመዝገብ የሚያስችል ስርዓት በሀገሪቱ እንደሌለ ጠቅሷል።

XS
SM
MD
LG