በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

የሱዳን ሽግግር መንግሥት የሁካቱ መባባስ እንዳሳሰበው ገለፀ


ፎቶ ፋይል፦ መቀሌ ከተማ
ፎቶ ፋይል፦ መቀሌ ከተማ

የሱዳን የሽግግር መንግሥት በአጎራባች ኢትዮጵያ ከሱዳን በምትዋሰነው የትግራይ ክልል ሁከቱ መባባሱ ያሳሰበው መሆኑን ገለፀ። ሁሉም ወገኖች ውጊያውን አቁመው ግጭቱን በሰላማዊ ድርድር እንዲፈቱ ተማጽኖ አቅርቧል።

የአካባቢው ሃገሮች እና ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ለአካባቢው ሰላምና መረጋጋት፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ሰላም እንዲወርድ ጥረት እንዲያደርጉ የሱዳን መንግሥት ተማጽኗል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ የሱዳን ከሰላ ክፍለ ግዛት ባለሥልጣናት ባለፉት ቀናት በኢትዮጵያ የትግራይ ክልል ውጥረቱ ማየሉን ተከትሎ ድንበራችንን ዘግተናል ሲሉ አስታወቁ።

የሱዳን ከሰላ ክፍለ ግዛት ተጠባባቂ አስተዳዳሪው ፋታል ራህማን አላሚን ከከሰላ በጥቂት ኪሎ ሚትር ርቀት ላይ በምትገኘው ትግራይ ክልል የሚካሄደው ውጊያ እስኪበርድ ድንበሩ ዝግ ሆኖ ይቆያል ብለዋል።

በሁለቱ ሃገሮች ወሰን ላይ በምትገኘው ወድ አል ሄሊዮ የድንበር ኬላ ቁጥጥር የሚያደርግ ኮሚቴ መስርተናል ብለዋል። ግጭቱን ሸሽተው የሚሰደዱ ሲቪሎችን ግን የሱዳን ባለስልጣናት በመቀበል እርዳታ ያደርጋሉ ብለዋል።

ሆኖም አንድም ቡድን ሱዳን ገብቶ ግዛታችንን የፍልሚያ ሜዳ እንዲያደርጋት አንፈቅድምም ያሉት የከሰላው ተጠባባቂ ሃገረ ገዢ፣ መሳሪያ የታጠቀ ሰው አናስገባም ሲሉም አክለዋል። ምንም ዓይነት ህገ ወጥ ስብሰባ አይፈቀድም፤ በሀገሩ የፀጥታ ችግር የፈጠረ አንድም ሰው መሳሪያ ታጥቆ ከሰላ እንዲገባ አንፈቅድም።

ከዛሬ ጀምሮ ድንበሩ ላልተወሰነ ጊዜ ዝግ ይሆናል ሲሉ አስታውቀዋል። የሱዳን የጸጥታ ኃይሎች የጦር ሰራዊቱን ጨመሮ ድንበሩን በንቃት እንዲጠብቁ ትዕዛዝ መሰጠቱን የከሰላው አስተዳዳሪ አመልክቷል።

በከተማዋ የሚገኙ የዐይን እማኞች ከተማዋ ላይ የጦር ሰራዊት በብዛት መሰማራቱን፣ የፈጣን ድጋፍ ኃይል የተባለው ሚሊሻ አባላትም ወደድንበሩ ሲጓዙ ማየታቸውን ተናግረዋል።

XS
SM
MD
LG