የሩስያ ፕሬዚዳንት ቪላዲሚር ፑቲን ሃገራቸው በሶሪያ አማፅያን ላይ የምታካሂደውን የአየር ድብደባ ሲቪሎች ዋና ከተማዋ ደማስቆ አቅራቢያ ውጊያው ከሚካሄድባቸው አካባቢዎች ማምለጥ እንዲችሉ በቀኑ ለአምስት ሰዓታት እንዲቋረጥ ማዘዛቸው ተዘግቧል።
የሩስያ የመከላከያ ሚኒስትር ሰርጌይ ሾይጉ በሰጡ መግለጫ ከነገ ማክሰኞ ጀምሮ ሩስያ ሲቪሎች ላይ ጉዳት እንዳይደርስ ስትል ጥቃቷን በሀገሩ ሰዓት ከጠዋቱ ሦስት ሰዓት እስከ ቀኑ ስምንት ሰዓት ድረስ ታቆማለች ብለዋል።
ፑቲን ይህን ትዕዛዝ ያስተላለፉት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታ ምክር ቤት በሙሉ ድምፅ በጠየቀው መሰረት በመላ ሶሪያ የአንድ ወር የተኩስ አቁም ሥራ ላይ ከዋለ ከሁለት ቀን በኋላ መሆኑ ነው።
ይሁን እንጂ ውጊያው ደማስቆ አቅራቢያ ምሥራቃዊ ጉታ ቀበሌ ቀጥሎ ዛሬ ቢያንስ አሥር ሰዎች ተገድለዋል የሚሉ ዘገባዎች አሉ። የአየር ጥቃቶችም ቀጥለዋል።
የፈረንሳይ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ከቱርክ ፕሬዚዳንት ሬቼፕ ታይብ ኤርዶዋን ጋር በስልክ ሲነጋገሩ በአማፅያን ይዞታ ሥር ባለችው ቀበሌ ሲቪሎችን እና ሆስፒታሎችን ዒላማ አድርጎ የሚካሄደው የአየር ድብደባ በከፍተኛ ደረጃ ያሳሰባቸው መሆኑን ገልፀውላቸዋል።
አንካራም በሰሜን ሶሪያ የአየር ድብደባዋን እንድታቆም የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ጠይቀዋል።
የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዥ ሲናገሩ የፀጥታው ምክር ቤት ያሳለፋቸው ውሳኔዎች ትርጉም የሚኖራቸው ተግባር ላይ ከዋሉ ብቻ ነው ብለዋል።
የፌስቡክ አስተያየት መስጫ