በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

የ“ሰማያዊ ቆብ ቀን” የተከበረው አፍሪካ ውስጥ ነው


አንቶኒዮ ጉቴሬሽ /የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ/ - ማዕከላዊ ማሊ ውስጥ ሞፕቲ ከተማ ውስጥ በተገኙበት ጊዜ፤ ግንቦት 22/2010 ዓ.ም. - ፎቶ - ማማዱ ቦኩም
አንቶኒዮ ጉቴሬሽ /የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ/ - ማዕከላዊ ማሊ ውስጥ ሞፕቲ ከተማ ውስጥ በተገኙበት ጊዜ፤ ግንቦት 22/2010 ዓ.ም. - ፎቶ - ማማዱ ቦኩም

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬሽ የዓለም ሰላም አስከባሪ ተልዕኮ ምሥረታ ሰባኛ ዓመትን ለማክበር ወደ ማሊ ሄደዋል። ምዕራብ አፍሪካዊቱ ማሊ ሚኑስማ በሚል ምኅፃር የሚጠራው የመንግሥታቱ ድርጅት ኃይል የሚገኝባት ሃገር ስትሆን ተልዕኮውን ለማጠናከር እንደሚሠሩ ዋና ፀሐፊው ቃል ገብተዋል።

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬሽ የዓለም ሰላም አስከባሪ ተልዕኮ ምሥረታ ሰባኛ ዓመትን ለማክበር ወደ ማሊ ሄደዋል።

ምዕራብ አፍሪካዊቱ ማሊ ሚኑስማ በሚል ምኅፃር የሚጠራው የመንግሥታቱ ድርጅት ኃይል የሚገኝባት ሃገር ስትሆን ተልዕኮውን ለማጠናከር እንደሚሠሩ ዋና ፀሐፊው ቃል ገብተዋል።

በዓለም ዙሪያ ግዳጅ ላይ ሳሉ በተገደሉ የድርጅቱ ወታደሮች ቁጥር እጅግ አቻ የሌለውን ሚኑስማን ይበልጥ ለማጎልበት እንዲቻልም ጉቴሬሽ የድጋፍ ጥሪ አሰምተዋል።

ግንቦት 21 ዓለምአቀፍ የሰማያዊ ቆብ ቀን ተብሎ ይታወቃል። ስለሰላም ቆመው ስለሰላም የወደቁ የዓለም አቃብያነ-ሰላም ወንዶችና ሴቶችን ለማሰብ፣ ጀብዱና ተጋድሏቸውን ለመዘከር በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የተደነገገ ቀን ነው። እናም የዘንድሮውን ዕለት ለማክበር ጠቅላይ ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬሽ ባማኮ የገቡ ጊዜ የመንግሥታቱ ድርጅት ቤተሰብ በመላ ግልብጥ ብሎ ወጥቶ ተቀበላቸው።

ማሊ የዓለም ልዑካን የነበሩ 172 ሰዎች የተገደሉባት ሃገር ነች። መቶው ባለ ሰማያዊ ቆብ ወታደሮች ነበሩ። የመንግሥታቱ ድርጅት ከተሠማራበት ሁሉ እንዲህ ዓይነት የበረታ ጉዳት በየትኛውም የምድር ጠርዝ አልደረሰበትም።

ማሊ 13 ሺህ አምስት መቶ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ወታደሮችን ለግዳጅ ተቀብላለች። በተጨማሪ ፈረንሣይ ለባርኻኔ ዘመቻዋ ያሰማራቻቸው ወታደሮች አሏት። የአውሮፓ ኅብረት ደግሞ የማሊን ወታደሮችና አጋዥ ክፍሎች ያሠለጥናል። ቡድን አምስት ወይም ጂ ፋይቭ ተብለው የሚጠሩት ማሊ፣ ኒዠር፣ ቡርኪና ፋሶ፣ ቻድና ሞሪታኒያ ደግሞ የራሣቸው የአካባቢው ፀጥታ አስከባሪ ኃይል አላቸው።

ማሊ እምብርት ላይ የሚገኘውን የጂ ፋይቭ ጠቅላይ ዕዝ ለመጎብኘት አንቶኒዮ ጉቴሬሽ ከትናንት በስተያ ጎራ ብለው ነበር።

የመንግሥታቱ ድርጅት ዋና ፀሐፊ ጉብኝታቸውን ባጠናቀቁ ጊዜ ለጂ ፋይቭ የፈጠነ ዓለምአቀፍ የገንዘብ ድጋፍ እንዲደርስ ጠይቀዋል። የድርጅታቸው ኃይል የተሰጠው ግዳጅ ሳህል አውራጃ ውስጥ ሽብርተኛ ንቅናቄዎችንና የተደራጀ ወንጀልን መዋጋት እንዲሁም ሲቪሉን ሕዝብ ከጥቃት መጠበቅ መሆኑን ለጋዜጠኞች የተናገሩት ጉቴሬሽ የኪሣቸው ነገር ግን በጣም አንገራጋሪ እንደሆነም አሳብቀዋል።

የማሊ ጠቅላይ ሚኒስትር ሱሜሉ ቡቤዬ ማይጋ ናቸው ጦራቸውን እየጎበኙ ሳሉ የክብር ዘቡ ሠላምታ የሚሰጣቸው።

ምንም እንኳ የማሊ የራሷ ወታደሮች ሠፈሩን ለማተራመስ ይንቀሳቀሳሉ ከሚባሉ ኃይሎች ጋር እየተዋጉ ቢሆንም የተሻለ ትጥቅ፣ ረቀቅ ያለ መሣሪያ ጠርቀም ያለ ደመወዝ ሊደርሱላቸው ይገባል። እስከዚያው ግን ማሊ ዳር ድንበሯን ለማስከበር፣ ሕዝቧንም ለመጠበቅ አጋዥ የሆኑት የውጭ ኃይሎች ጫማ እየረገጣት ይቆያል።

እነዚያ ባዕዳን ጦሮች ታዲያ በተለይ ደግሞ የመንግሥታቱ ድርጅት የማሊ ልዑካን የራሣቸውን ደኅንነት ለመጠበቅ የሚያስችሏቸውን እርምጃዎች እያጠናከሩ እንደሚቀጥሉ ጉቴሬሽ አስታውቀዋል።

የመንግሥታቱ ድርጅት የማሊ ተልዕኮ ሚኑስማ የሠፈረበት የቲምቡክቱ አየር ጣቢያ ባለፈው ሚያዝያ ውስጥ ድንገት በተከፈተበት አስደንጋጭ ጥቃት መመታቱ ወታደሮቹ ምን ያህል ለአደጋ የተጋለጡ እንደሆነ ማስታወሻ ሰጥቶናል ብለዋል አንቶኒዮ ጉቴሬሽ።

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ባማኮ ውስጥ ጥብቅ የሆነ የቅኝት ሥርዓቶችን እንደሚዘረጋ፣ የተራቀቁ የማስጠንቀቂያ መዋቅሮችንና በሃገሪቱ ሰሜን በሚገኙ አንዳንድ የጦር ሠፈሮች ውስጥ ራዳሮች እንደሚተከሉ፤ ቦምቦችንና የተቀበሩ ፈንጂዎችን ለማደንም አነፍናፊ ውሾች እንደሚሠማሩ፤ የአካባቢ ቅኝትና የአደጋ ማስጠንቀቂያ የተጠናከሩ ሥልጠናዎች እንደሚሰጡ የተናገሩት ጉቴሬሽ ተራራ ሸንተረሩን ለመጠበቅና ተቆጣጥሮ ለመቆየት የሚያስችሉ በርካታ ዘመቻዎች እንደሚካሄዱ አስታውቀዋል።

እና ይህ በቂ ይሆናል? ብዙው እንግዲህ የሚወሰነው ለማሊ፣ ለሚኑስማ እና ለጂ ፋይቭ የሳህል ኃይል ከዓለምአቀፉ ድጋፍ ከሚገኘው የገንዘብ መጠን ይሆናል።

አሁን ግን እጅግ የከፋው የካዝና መመናመን ለወደፊቱ የከበዱ ችግሮችን የደገሠ ነው። “ማሊ ብትወድቅና ብትሰበር፤ ስብርባሪዋና ፍንጥርጣሪዋ መከራን የሚዘራው ለማሊ ጎረቤቶች ብቻ ሳይሆን - አሉ ጉቴሬሽ፤ መዘዙ ከሳህል እስከ መላ ሜዲቴራኒያን ክልልና ዘልቆም ወደ አውሮፓ ጠልቆ የሚጎዳ ይሆናል።”

ሽብር ፈጠራ ሽብር ፈጥሮ በግርግሩ ውስጥ ከመተራመስ ይልቅ የሽብርተኝነትን ችግር ከፅንሱ መከላከል ይበጃል - ሲሉ መክረዋል የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬሽ።

የተያያዘውን የድምፅ ፋይል ያዳምጡ።

የ“ሰማያዊ ቆብ ቀን” የተከበረው አፍሪካ ውስጥ ነው
please wait

No media source currently available

0:00 0:05:27 0:00

የፌስቡክ አስተያየት መስጫ

XS
SM
MD
LG