በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ላቭሮቭ በዓለም ዙርያ ተከሰተ ላሉት ቀውስ ምዕራባዊያንን ተቹ


ላቭሮቭ በዓለም ዙርያ ተከሰተ ላሉት ቀውስ ምዕራባዊያንን ተቹ
please wait

No media source currently available

0:00 0:03:17 0:00

በአፍሪካ የአራት ሃገሮች ጉብኝታቸው ማብቂያ ላይ ትናንት ኢትዮጵያ የገቡት የሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌይ ላቭሮቭ ዛሬ ከኢትዮጵያ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ጋር ተገናኝተው የሁለትዮሽ በተባሉ ጉዳዮች ላይ መክረዋል።

ሚስተር ላቭሮቭ ዛሬ ጠዋት ኢትዮጵያ ውስጥ ከሚገኙ የዲፕሎማቲክ ማኅበረሰብ አባላት ጋር ሲነጋገሩ የዩክሬን ጦርነት ከተጫረ ወዲህ በመላ ዓለም ተከስቷል ላሉት የኢኮኖሚ ምስቅልቅል ምዕራባውያንን ተጠያቂ አድርገዋል።

በተለይ ለምግብና ለማዳበርያ ዋጋ መናር መንስዔው “የሩሲያን ልዩ ዘመቻን ተከትሎ በአውሮፓ ሃገሮችና በዩናይትድ ስቴትስ የተወሰደ ያለ እርምጃ ነው” ብለዋል።

“አዎ፤ በርግጥ ዩክሬን ውስጥ የተከሰተው ሁኔታ በምግብ ዋጋ ላይ ጫና አሳድሯል። ነገር ግን ችግሩ የተፈጠረው ሩሲያ በዩክሬን ላይ በከፈተችው ልዩ ዘመቻ ምክንያት ሳይሆን በምዕራባዊያን በግድየለሽነት በተወሰደ እርምጃ ምክንያት ነው።

በተለይ በሩሲያ ላይ ማዕቀብ በመጣል ያመጡት ጣጣ ነው። ይሄንን ስናብራራላቸው ማዕቀቡ ምግብንና ማዳበርያን የሚያካትት አይደለም ይሉናል። በርግጥ ማዕቀቡ ምግብና ማዳበርያ ወደዓለም ገበያ መላክን አይጨምርም፤ ነገር ግን ማዕቀቡ የሩሲያ መርከቦች የሜዲቴራኒያን ባህርን እንዲያቋርጡ አይፈቅድም። የሌሎች ሀገሮች መርከቦች ወደ ሩሲያ ወደብ ተጠግተው እንዳይጭኑ ይከለክላል። የሩሲያ መርከቦች መድኅን ዋስትና እንዳያገኙ ክፍያው በጣም አሻቅቧል።

በመጨረሻም የአገልግሎት ክፍያዎቹን የሚያከናውነው የሩሲያ የግብርና ባንክ በአውሮፓ ኅብረት በተጣለው ማዕቀብ ውስጥ ተካትቷል” ብለዋል ላቭሮቭ።

ከዩክሬኑ ቀውስ ሌላ የዓለምን የምግብና የማዳበርያ ዋጋ ያናረው የኮቪድ-19 ወረርሽኝ መሆኑንም ሚስተር ላቭሮቭ በሩሲያ ኤምባሲ ውስጥ ለዲፕሎማቶቹ በሰጡት ማብራሪያ አመልክተዋል።

በተለይ “የመግዛት አቅማቸው ከፍተኛ የሆነ ሀገሮች የወረርሽኙን መቀስቀስ ተከትሎ የፈፀሙት የምግብ ግዥ ለዋጋው መናር አንዱ ምክንያት ሆኗል” ብለዋል።

አሁንም መላ እንዲበጅ ቱርክና የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ ሽምግልና ላይ መሆናቸውን ላቭሮቭ ጠቁዋል። “ውጤቱን አብረን አብረን እንጠብቃለን” ብለዋል።

የሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌይ ላቭሮቭ ከዲፕሎማቲክ ማኅበረሰብ አባላት ጋር የነበራቸውን ውይይት ካጠናቀቁ በኋላ ከኢትዮጵያው አቻቸው ደመቀ መኮንን ጋር ተገናኝተው ተነጋግረዋል።

ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከሚስተር ላቭሮቭ ጋር መመካከራቸውን የሃገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

በሁለቱ ሀገሮች መካከል ያለው ግንኙነት ታሪካዊ መሆኑን የሩሲያው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አስታውሰው አሁንም ሩሲያና ኢትዮጵያ ያላቸውን የንግድና ወታደራዊ ግንኙነቶቻቸውን ለማጠናከር መነጋገራቸውን መገናኛ ብዙኃኑ ዘግበዋል።

ሚስተር ላቭሮቭ ከኢትዮጵያ ፕሬዚዳንት ሳኅለወርቅ ዘውዴ ጋር መገናኘታቸውን የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የገለፀ ሲሆን ማምሻውንም የኢትዮጵያ ጉብኝታቸውን አጠናቅቀው ወደ ሃገራቸው መመለሳቸውን አስታውቋል።

XS
SM
MD
LG