በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

የየመን ተፋላሚዎች በተመድ መሪነት ሊነጋገሩ መስማማታቸውን የባህረ ሰላጤው ሀገራት ተቀበሉ


የየመን ካርታ
የየመን ካርታ

የየመን ተፋላሚ ወገኖች የተኩስ አቁም እርምጃ ለመውሰድ እና በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት መሪነት የሚካሄድ የሰላም ድርድር ላይ ለመሳተፍ ቃል መግባታቸውን፣ ሳዑዲ አረብያን ጨምሮ የባህረ ሰላጤው አረብ ሀገራት አወድሰዋል።

በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን የገደለውን እና በዓለም ላይ ካሉት አስከፊ ሰብዓዊ ቀውሶች መካከል አንዱ የሆነውን ደም አፋሳሽ ግጭት ለማስቆም ሲካሄድ በቆየው በቅርብ ጊዜው ጥረት የተደረሰውን ሥምምነት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የየመን ልዩ መልዕክተኛ ሃንስ ግራንድበርግ ይፋ አድርገዋል፡፡

እ.አ.አ በ2014 በኢራን የሚደገፉት ሁቲዎቹ አማጽያን ሰንዓን ከተቆጣጠሩ ወዲህ በአረብ ባህረሰላጤ በድህነቷ የምትታወቀው ሀገር በጦርነት ስትታመስ ቆይታለች።

እ.አ.አ ባለፈው 2022፣ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አደራዳሪነት የተካሄደ የተኩስ አቁም ጦርነቱ እንዲቀንስ ቢያግዝም፣ የስምምነቱ ቀነ ገደብ በጥቅምት ወር አብቅቷል። በግጭቱ ውስጥ ቁልፍ ሚና ያላት ብቸኛ የውጭ ሀገር የሆነችው ሳዑዲ አረብያ፣ የመንግሥታቱ ድርጅት ከትናንት በስተያ ቅዳሜ ይፋ ያደረገውን "የሰላም ጎዳና ለመደገፍ የሚያስችል ፍኖተ ካርታ" በደስታ ተቀብላዋለች።

የሳዑዲ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርም የየመን ተፋላሚ ወገኖች "በመንግሥታቱ ድርጅት ስር በጠረጴዛ ዙሪያ ተቀምጠው እንዲደራደሩ እና ሁሉን አካታች እና ዘላቂ የፖለቲካ መፍትሔ ላይ እንዲደርሱ" ሲል አበረታቷል።

ከአደራዳሪዎቹ መካከል አንዷ የሆነችው ኦማንም የድርድሩን ሀሳብ በደስታ ተቀብላ "በተቻለ ፍጥነት ስምምነት እንዲፈረም" ያላትን ተስፋ ገልጻለች።

ካታርም በተመሳሳይ መልኩ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት፣ ሳዑዲ አረብያ እና ኦማን ለሰላም ስላደረጉት ግፊት አመስግና፣ ተፋላሚዎቹ ወገኖች የሰላም ሥምምነቱን እንዲያፋጥኑ ጠይቃለች።

መድረክ / ፎረም

XS
SM
MD
LG