በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

የመጀመሪያ ዙር የኮቪድ ክትባት በጋና


ጋና በዓለም ጤና ድርጅት አማካኝነት የተላከውን የመጀመሪያውን ዙር የኮቪድ-19 ክትባት ተቀበለች፡፡

ጋና የክትባት መድሃኒቶች የተቀበለችው አነስተኛና መካከለኛ ገቢ ላላቸው የዓለም አገሮች የክትባት መድሃኒት ለማጋራት በተቋቋመው ዓለም አቀፍ መርሃግብር መሰረት ነው።

ስድስት መቶ ሺህ የአስትራዜኔካ-ኦክስፎርድ ዩኒቨርስቲ ክትባቶችን የጫነው አውሮፕላን ዛሬ ከመዲናዋ አክራ መግባቱን የተባበሩት መንግሥታት ዓለም አቀፍ የህፃናት ድርጅት /ዩኒሴፍ/ የአስቸኳይ ዕርዳታ ፕሮግራም ነው ይፋ ያደረገው።

ክትባቶቹ የተመረቱት በዓለም ትልቁ የክትባት አምራች ኩባንያ የህንዱ ሴረም ኢንስቲትዩት ነው፡፡

ወደ ጋና የተላከው ክትባት የተገዛው ኮቫክስ በመባል በሚታወቀው የዓለሙጤና ድርጅት የወረርሽኝ መከላከያ ዝግጅት ማስተባበሪያ ፕሮግራም፤ በበጎ አድራጎት ሥራ በተሰማራው የቢል እና ሜሌንዳ ጌትስ ተቋም የሚረዳው የክትባቶች ስርጭት ህብረት የተባለው ድርጅት ዓለምቀፍ ትብብር አማካኝነት ነው።

በዓለም ጤና ድርጅት አስተባባሪነት የተጠነሰሰው ይህ ፕሮጀክት በበለፀጉ አገራት እገዛ ክትባቶችን በመግዛት ለሁሉም ሃገሮች በተመጣጠነ መንገድ ለማሰራጨት ያቅዳል።

ኮቫክስ መጠኑ ሁለት ቢሊዮን የሚደርስ ክትባት “ተስፋ የተጣለባቸው” የተባሉ ክትባቶችን በመስራት ላይ ከሚገኙ ኩባኛዎች ማግኘት የሚችልበት ስምምነት መደረሱን የዓለም ጤና ድርጅት ባለፈው የታህሳስ ወር ይፋ ማድረጉ ይታወሳል።

በተመሳሳይ የዩናይትድ ስቴትሱ ፕሬዚዳንት ጆ ቢደን ባለፈው ሳምንት ለኮቫክስ ፕሮግራም የሚውል 4 ቢሊዮን ዶላር ለመለገስ ቃል መግባታቸው ተዘግቧል።

XS
SM
MD
LG