በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ቻይና የቡድን 7 አገራትን የአቋም መግለጫ አወገዘች


የቡድን 7 መሪዎች
የቡድን 7 መሪዎች

በቡድን 7 አገራት የተካሄደው ጉባኤ “ጸረ ቻይና ዎርክሾፕ” ነው ሲል በቻይና የሚደገፈውና ግሎባል ታይምስ የተሰኘው ጋዜጣ ዛሬ በርዕሰ አንቀጹ ጽፏል።

በሂሮሺማ ጃፓን የተሰባሰቡት የቡድን 7 አገራት ቅዳሜ ዕለት ያወጡትን የአቋም መግለጫ ተከትሎ፣ ቻይና በአገሪቱ የሚገኙትን የጃፓን አምባሳደር ጠርታ ስታነጋር፣ በእንግሊዝ የሚገኘው የቻይና ኤምባሲ ደግሞ አገሪቱ የቻይናን ስም ከማጥፋት እንድትቆጠብ ጠይቋል።

የቡድን 7 አገራቱ ቅዳሜ ዕለት ባወጡት የአቋም መግለጫ፣ ቻይና በታይዋን ላይ የምታደርገውን ዛቻ፣ የኑክሌር ትጥቋን በተመለከተ እንዲሁም በዓለም ኢኮኖሚ ላይ አላት ያሉትን አሉታዊ ተጽእኖ አውግዘዋል።

“ቡድን 7 ወደ ጸረ ቻይና ዎርክሾፕነት ወርዷል” በሚል ርዕስ ግሎባል ታይምስ ባወጣው ርዕሰ አንቀጽ፣ አሜሪካ በምዕራቡ ዓለም ጸረ ቻይና መረብ ለመዘርጋት እየጣረች ነው ብሏል።

የቻይናው የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር የቡድን 7 አገራቱ ያወጡትን መግለጫ መቃወሙን አስመልክቶ፣ በአገሪቱ የሚገኙትን የጃፓን አምባሳደር ጠርቶ አነጋግሯል።

በዩክሬን ላይ በምታካሂደው ጦርነት ምክንያት በቡድን 7 ጉቤኤ ላይ የተወገዘችው ሩሲያም፣ ጉባኤው “የጸረ ሩሲያና የጸረ ቻይና አቋሞች መፈልፈያ ነው” ብላለች፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን ከቻይና ጋር ያለው የሻከረ ግኑኝነት በቅርቡ ይሻሻላል ብለው እንደሚጠብቁ ተናግረዋል።

ቤጂንግ የቡድን ሰባቱን መግለጫ በተመለከተ ፈጣን ምላሽ በሰጠችበት ሁኔታ፣ ውጥረቱ ወዲያውኑ ይረግባል ብለው እንደማይጠብቁ ተንታኞች በመናገር ላይ ናቸው።

XS
SM
MD
LG