በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ሞቃዲሾ ላይ በተጣለ ጥቃት ብዙ ጉዳት ደረሰ


ሶማሊያ ዋና ከተማ ሞቃዲሾ ውስጥ በሚገኝ ሰው የሚበዛበት አንድ ምግብ ቤት ላይ ማምሻውን በተከፈተ የፍንዳታና የተኩስ ጥቃት ቢያንስ ሰባት ሰው መገደሉ ተገለፀ፡፡

ይህንን ኢትዮጵያዊያን እንደሚሠሩበትና እንደሚገለገሉበት የተነገረ ምግብ ቤት ብዙ የውጭ ሰዎችና የመንግሥት ሠራተኞች እንደሚያዘወትሩት ታውቋል፡፡

ቡድኑ እስከአሁን ኃላፊነት በይፋ ባይወስድም የአልሻባብ ታጣቂዎች መሆናቸው የተጠረጠረው ጥቃት አድራሾች በቅድሚያ በሆቴሉ ደጃፍ ላይ አንዲት መኪና ላይ የተጠመደ ፈንጂ ካፈነዱ በኋላ በግማሽ ደቂቃ ጊዜ ውስጥ መሣሪያ የታጠቁ ሰዎች ሆቴሉ ውስጥ ገብተው ተኩስ መክፈታቸውን የዐይን እማኞች ለቪኦኤ ተናግረዋል፡፡

በሥፍራው ፈጥነው ከደረሱ ጋዜጠኞች መካከል የነበረው የቪኦኤ የሞቀዲሾ ሪፖርተር እራሱ ሰባት አስከሬኖችን ወድቀው ማየቱን አመልክቷል፡፡

በሕንፃው ላይ የደረሰው ጉዳት እጅግ ከፍተኛ መሆኑንና ብዙ ሰው ወይም አስከሬንም ከፍርስራሹ ሥር ሊኖር እንደሚችል ተናግሯል ሪፖርተሩ፡፡

ሕንፃው ውስጥ ከምግብ ቤቱ በተጨማሪ የውበት ሳሎን፣ የማሳጅ ማዕከልና የሁካ ወይም ሺሻ ቤት እንደሚገኝበት ታውቋል፡፡

አሁን ከሕንፃው ውስጥ ተኩስ ባይኖርም አካባቢውን ለማፅዳትና የተረፉትን የማውጣት ሥራ ለመጀመር እየተጣደፉ መሆናቸውን የሶማሊያ ፖሊስ መኮንን የሆኑት አደን ሞሐመድ ለቪኦኤ ተናግረዋል፡፡

የፌስቡክ አስተያየት መስጫ

XS
SM
MD
LG