ከቀድሞ የኢትዮጵያ ብረታ ብረት እና ኢንጅነሪንግ ኮርፖሬሽን (ሜቴክ) ዋና ዴሬክተር ሜጄር ጀነራል ክንፈ ዳኘው ክስ ጋር በተያያዘ ለምስክርነት የተጠሩትና ታስረው ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ ትዕዛዝ የተላለፈባቸው የቀድሞው የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማሪያም ደሳለኝ በአካል መቅረብ እንደማይችሉ ለፍርድ ቤት በደብዳቤ አስታወቁ።
አቶ ኃይለማርያም እስካሁን ከፍርድ ቤት የደረሳቸው እና ፈርመው የተቀበሉት መጥሪያ እንደሌለ በደብዳቤያቸው ጠቁመው ፍርድ ቤት በጠራቸው በማንኛውም ጊዜ ግን ምስክርነት ለመስጠት ዝግጁ መሆናቸውን እንደገለጹም ከተከሳሹ ጠበቃ አንዱ ለአሜሪካ ድምፅ ተናግረዋል።
መደበኛ ሥራቸው እና ኑሮዋቸው በውጭ ሀገር መሆኑን አመለክተው፣ ካሉበት በቪዲዮ ኮንፈረንስ ምስክርነት እንዲሰጡ መጠየቃቸውን እና በከሳሽ እና ተከሳሽ ወገን ተቀባይነት ማግኘቱን ጠበቃው አብራርተዋል። ሜጄር ጀነራል ክንፈ ዳኘው ከታሠሩ ሦስት ዓመት ከአራት ወራት ተቆጥሯል።
ዝርዝር ዘገባውን ከተያያዘው ፋይል ያዳምጡ።