በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ስለ ማክሮን ድል የዓለም ምላሽ


ኢማኑኤል ማክሮን
ኢማኑኤል ማክሮን

በፈረንሣይ ምርጫ አክራሪዋ ብሔረተኛ ማሪን ሎ ፔን በተቀናቃኛቸው ኢማኑኤል ማክሮን ድል መነሣታቸው በይፋ ከተገለፀ ገና ሁለት ቀን መሆኑ ነው፡፡

በፈረንሣይ ምርጫ አክራሪዋ ብሔረተኛ ማሪን ሎ ፔን በተቀናቃኛቸው ኢማኑኤል ማክሮን ድል መነሣታቸው በይፋ ከተገለፀ ገና ሁለት ቀን መሆኑ ነው፡፡

በምርጫው ውጤት ላይ በዓለም ዙሪያ የሚስተጋባው ምላሽ እየጎረፈ ነው፡፡

በሃገራቸው የአውሮፓ ኅብረት አባልነት ላይ ሁለቱ መሪዎች ያላቸው አቋም ፍፁም የሚጣረስ ሲሆን ሎ ፔን ፈረንሣይ ከኅብረቱ እንድትወጣ አደርጋለሁ ሲሉ ቆይተዋል፤ ወጣቱ መሐልተኛ ፖለቲከኛ ማክሮን ግን የኅብረቱ ወዳጅ ናቸው፤ ብዙ ጥያቄዎች ቢኖሯቸውም፡፡

“IT IS A BOY!! ወንድ ልጅ ከነቃጭሉ!!” ይላል አንድ የጀርመን ጋዜጣ ድፍን አውሮፓና አሜሪካንም፤ የፈረንሣይ ጉዳይ ይመለከተኛል የሚል ሌላውንም ዓለም ሁሉ ላስማጠው የፈረንሣይ የምርጫ ውጤት ዘገባ የሰጠው ርዕስ፡፡

«አውሮፓ አሸነፈች» አለ ሌላው ደግሞ፡፡

ስለ ማክሮን ድል የዓለም ምላሽ
please wait

No media source currently available

0:00 0:03:47 0:00

እንዲያው መንገድ ላይ ከሚተራመሰው ሰው መካከል በኢማኑኤል ማክሮን ግዙፍ ድል እፎይታ የተሰማቸው ብዙ ቢሆኑም፤ በዘንድሮው ምርጫ፤ ምርጫ በማጣታቸው የቆዘሙም ጥቂት አይደሉም፡፡

«መጨረሻው እንዲህ መሆኑ አሳዝኖኛል፡፡ ምክንያቱም ማክሮን የሁሉም ሰው ምርጫ አይደሉም፡፡ ለአውሮፓ ግን መልካም ሆኖላታል፡፡ ለማንኛውም ሎ ፔን ባለማሸነፋቸው አምላክ ይመስገን» ብላለች ከፈረንሣዊያን መራጮች አንዷ ሳንድራ ባን፡፡

የጀርመን ቻንስለር አንጌላ መርከል የማክሮንን ድል ዜና እንደሰሙ ስልካቸውን ብድግ አድርገው ተመራጩ ፕሬዚዳንት ዘንድ ለመምታት ጊዜ አልወሰደባቸውም፡፡

«ኢማኑኤል ማክሮን በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ፈረንሣዊያንን፤ እንዲሁም የብዙ ጀርመናዊያንን፤ እንዲሁም የመላዪቱን አውሮፓ ተስፋ የተሸከሙ ሰው ናቸው፡፡ ደፋር የሆነ አፍቃሬ-አውሮፓ ዘመቻ ነው ያካሄዱት፡፡ ለዓለም ክፍት መሆን እንደሚያስፈልግ የሚያምኑ ሰው ናቸው፡፡ ለማኅበራዊ ገበያ ምጣኔ ኃብትም በፅናት የቆሙ ናቸው» ብለዋል መርከል፡፡

ኢስቶኒያ ዋና ከተማ ታሊን ላይ የተሰበሰቡ የባልቲክ ሃገሮችና የፖላንድ መሪዎች የማክሮንን ድል በፀጋ መስማታቸውን አሳውቀዋል፡፡ የሊትዋንያው ጠቅላይ ሚኒስትር ሳዉሊዩስ ስክቬርኔሊስ «የፈረንሣይ ምርጫ ውጤት የሚናገረው የተባበረች አውሮፓ፣ የምትበለፅግ አውሮፓ፣ ደኅንነቷ የተጠበቀ አውሮፓ፤ በግዙፍ እሴቶቿ ላይ ተመርኩዛ፣ ሰብዓዊ መብቶችን በማክበሯ ላይ ፀንታ መፃዒ ዕጣዋ ብሩህ ነው» ብለዋል፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ ለንደን ላይ የቅስቀሳ ዘመቻ ሲያደርጉ የነበሩት የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ቴሬሣ ሜይ ሲናገሩ ሃገራቸው ከአውሮፓ ኅብረት በምትወጣባቸው ድርድሮች ላይ እጆቻቸውን እንደ ማክሮን ሁሉ ጠንካራ ሊያደርግላቸው የሚችል ሥልጣን መራጮች እንዲሰጧቸው ጠይቀዋል፡፡ «እንግሊዝ ውስጥም ወደ ድርድሩ ጠረጴዛ ጠንካራ አቋም ይዘን መቅረብ የሚያስችለን አቅም ያለን መሆኑን ማረጋገጥ አለብን» ብለዋል ሜይ ዛሬ ሲናገሩ፡፡

የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትረምፕ ማክሮንን «ለታላቁ ድልዎ እንኳን ደስ አለዎ» ለማለት የመረጡት የትዊተር አካውታቸውን ነው፡፡ አብረው ለመሥራትም ብርቱ ፍላጎት እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡

ከመራጭ የ66 ከመቶውን ድምፅ ያሸነፉት ማክሮን እኮ ማን እንደሆኑ እንኳ የዛሬ አምስት ዓመት ከፈረንሣዊያን የሚያውቅ ቢኖር የቅርብ ጓደኞቻቸውና ቤተሰቦቻቸው ነበሩ፡፡ ዛሬ ፈረንሣይን የምታክል ታላቅ ሃገርና ግዙፍ ምጣኔ ኃብት የማሽከርከር ትልቅና ከባድ ፈተና ተደቅኖባቸዋል «ስለዚህም ተከታዩ የሃገር ውስጥ ፈተናቸው በፓርላማቸው ውስጥ በቂ መቀመጫዎችን ማሸነፍ ነው የሚሆነው፡፡ ከዚያ በኋላም አከናውናለሁ ብለው ቃል የገቡባቸውን ጉዳዮች ለማሳካት በሕግ መወሰኛ ምክር ቤቱ ውስጥ በቂ ድጋፍ ማግኘት ይኖርባቸዋል» ሲሉ የካርኔጊ የዓለምአቀፍ ሰላም ጥናት ተቋሙ ባልደረባ ኤሪክ ብራትበርግ ሃሣባቸውን ለቪኦኤ በስካይፕ አካፍለዋል፡፡

ማክሮን ሰሞኑን በሚጠሩት የሰሜን አትላንቲክ የጦር ትብብር ድርጅት፤ ኔቶ እና ሰባቱ ባለጠጋ ሃገሮች ቡድን፤ ጂ-7 ጉባዔዎች ወቅት በዓለም አቀፍ መድረኮች ላይ ምን ዓይነት የአመራር ዓይነትና ብቃት እንደሚኖራቸው ይታያል ብለዋል ብራትበርግ፡፡

ለተጨማሪ የተያያዘውን የድምፅ ፋይል ያዳምጡ።

ስለ ማክሮን ድል የዓለም ምላሽ
please wait

No media source currently available

0:00 0:04:31 0:00

የፌስቡክ አስተያየት መስጫ

XS
SM
MD
LG