ወይዘሪት ብርቱካን ሚደቅሳ ላለፉት አንድ አመት ከዘጠኝ ወር ከታሰሩበት ወህኒ ቤት የተለቀቁት ማክሰኞ ከረፋዱ 5ሰአት ላይ ነበር።
ከተወለደች ጀምሮ አራት የእድገት አመቷን ከእናቷ ተለይታ ያሳለፈችው የ6አመት ልጃቸውና ከእናታቸው ጋር ሆነው በወህኒ ቤት መኪና ወደ ቤታቸው ሲደርሱ ከ500 በላይ ደጋፊዎቻቸውና ወዳጅ ዘመዶቻቸው አቀባበል አድርገውላቸዋል።
የቅንጅት መሪዎች ከእስር የተፈቱበትን የይቅርታ ህግ ጥሰዋል በሚል በታህሳስ ወር 2001 ዓም ወይዘሪት ብርቱካን ሚደቅሳ ከታሰሩ ጀምሮ በርካታ የአለም አቀፍ ተቋማት፣ መንግስቶችና የፖለቲካ ድርጅቶች ብርቱካን ከእስር እንዲፈቱ ሲወተውቱ ቆይተዋል።
በአለም ዙሪያ የሰብአዊ መብት አጠባበቅን እየተከታተለ የሚመዘግበው አምነስቲ ኢንተርናሽናል በዛሬውለት ባወጣው መግለጫ ከ21 ወራት እስራት በኋላ የብርቱካን ሚደቅሳ መፈታት እንዳስደሰተው ገልጾ፤ መጀመሪያውኑም ወይዘሪት ብርቱካን መታሰር አልነበረባቸውም ይላል።
“ብርቱካን ሚደቅሳ አመጽ በሌለበት መልኩ ሃሳብዋን በመግለጽዋ ብቻ የታሰረች የህሊና እስረኛ መሆንዋ፣ ገልጾ ነበር። እንድትፈታም ደግመን ደጋግመን ስንጠይቅ ነበር፣ መበፈታትዋ እጅግ ደስ ብሎናል” ሲሉ ሚሸል ካጋሪ የአምነስቲ የአፍሪካ ክፍል ምክትል ስራአስኪያጅ ለቪኦኤ ተናግረዋል።
መለስካቸው አምሃ ከአዲስ አበባ፣ ሔኖክ ሰማእግዜር ከዋሽንግተን ዲሲ ያጠናቀሩትን ዘገባ ያዳምጡ።