አዲስ አበባ —
የኢትዮጵያ ሣይንስ አካዳሚ “የኢትዮጵያ ከፍተኛ ትምህርትና ምርምርን ወደላቀ ደረጃ ማሳደግ” በሚል መሪ ቃል ዛሬ ሁለተኛ የሣይንስ ጉባዔውን ከፍቷል፡፡
በአዲስ አበባው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአፍሪካ አዳራሽ በተከፈተው በዚህ ጉባዔ ላይ ትኩረት ይሰጣቸዋል የተባሉ ጉዳዮች በከፍተኛ ትምህርት ሃገር ወይም ኅብረተሰብ የሚያገኙት ጥቅም የሚያድግባቸው መንገዶች፣ የከፍተኛ ትምህርትን ጥራት እንዴት ማሻሻልና እንዴት ከልማት ጋር ማቆራኘት እንደሚቻል፤ እንዲሁም በምርምርና ዕውቀት በማመንጨት ላይ ያተኮሩ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትን ማቋቋም ወይም ማጠናከር የሚሉ እንደሆኑ ተጠቁሟል፡፡
ዛሬ በሃገሪቱ ውስጥ እየተስፋፋ ካለው ከፍተኛ ትምህርት አንፃር የምርምርና የትምህርት ጥራቱ የተመጣጠኑ አለመሆናቸውን የአካዳሚው ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር ማስረሻ ፈጠነ ተናግረዋል፡፡
ጉባዔው የከፍተኛ ትምህርትን ጥራት ለማሻሻልና በምርምር ላይ ያተኮሩ ዩኒቨርሲቲዎች የሚቋቋሙበትንና የሚጠናከሩበትንም የፖሊሲ ሃሣብ ለመንግሥት እንደሚያቀርብ ተገልጿል።
ለተጨማሪ የመለስካቸው አምሃን ዘገባ ከተያያዘው የድምፅ ፋይል ያዳምጡ፡፡