በሱዳን ይካሄዳል ያሉትን የጾታ ጥቃት የተቃወሙ የሱዳን ሴቶች ትናንት እሁድ ካርቱም በሚገኘው በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ጽ/ቤት ፊት ለፊት ተሰልፈዋል፡፡
ተቃዋሚዎቹ ግጭት በሚካሂድባቸው የሱዳን አካባቢዎች የተሻለ የሴቶችና ህጻናት ደህንነት ጥበቃ፣ ፍትህና ተጠያቂነት እንዲኖር ጠይቀዋል፡፡
ጥቁር የለበሱ በርካታ ሴቶች የታዩበት የተቃውሞ ሰልፍ ላይ የተለያዩ መፈክሮችን ያነገቡት ሴቶች፣ የሱዳን ወታደራዊ አገዛዝ የሴቶችን ደህንነት እንዲጠብቅና ሥልጣንን ለህዝብ እንዲመልስ ጠይቀዋል፡፡
በጥቅምት ወር ውስጥ በብሉ ናይል እና በምዕራብ ኮርዶፋን ግዛቶች እንደገና ባገረሸው የማኅበረሰብ ግጭት ቢያንስ 170 የሞቱበትና 300 ደግሞ የቆሰሉበት መሆኑን በሱዳን የሚገኘው የተባበሩት መንግሥትት ድርጅት አስታውቋል፡፡
በትንሹ 1ሺ 200 የሚሆኑ ቤተሰቦች መበተናቸውን የገለጸው የመንግሥታቱ ድርጅት ባወጣው መግለጫ የሴቶችና ህጻናት ደህንነት እንዲጠበቅ አሳስቧል፡፡