የሱዳን ሴቶች የማኅበረሰብ አንቂ አሚራ ኦስማን ሀመድ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የሰብአዊ መብት ግንባር ቀደም ተከላካይ አሸናፊ ሆና መመረጧን ዓለም አቀፉ ድርጅት ዛሬ ዓርብ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
በ40ዎቹ ዓመታት ውስጥ የምትገኘው አሚራ፣ ለሁለት አስርት ዓመታት ለሱዳን ሴቶች መብት ስትሟገት የቆየች ሲሆን በዚህ ዓመት በሱዳን የተካሄደውን መንፈንቅለ መንግሥት ተከትሎ በተነሳው ህዝባዊ ተቃውሞ ሳቢያ ታስራለች፡፡
አሚራ በዚህ ዓመት እኤአ የ2022 የዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶች ግንባር ቀደም ተከላካይ አሸናፊዎች በመሆን ከአፍጋኒሲታን፣ ቤላሩስ፣ ዚምባቡዌና ሜክስኮ ከተመረጡት አንዷ ሆናለች፡፡ አሚራ እኤአ በ2009 “የሴቶች ጭቆና ይብቃ” የሚል ንቅናቄ መጀመሯ ተነግሯል፡፡
ባላፉት አስር ዓመታት ውስጥም በተለያዩ ጊዜያት እየታሰረች መፈታቷ ተገልጿል፡፡ ባላፈው ጥር ወር 30 የሚደርሱ ፊታቸውን የተሸፈኑ ታጣቂዎች፣ ካርቱም ከሚገኘው መኖሪያ ቤቷ፣ በሌሊት አፍነው ወዳልታወቀ ቦታ እንደወሰዷትም ተመልክቷል፡፡