ሜክሲኮ ውስጥ አንድ ጋዜጠኛ ትናንት ሰኞ በጥይት ሲገደል በዚህ ዓመት ብቻ ሃገሪቱ ውስጥ የተገደሉትን ጋዜጠኞች ቁጥር 15 አድርሶታል። ግሬሮ በምትባለው ደቡባዊ ግዛት “የግሬሮ እውነታ” የሚል ፕሮግራም ያዘጋጅ የነበረው ፍሬዲድ ሮማን በአብዛኛው በግዛቲቱ ፖለቲካ ላይ ያተኮሩ ዘገባዎችን የሚያቀርብና አምደኛም እንደነበረ አሶሲየትድ ፕረስ አመልክቷል።
ግሬሮ የአደንዛዥ ዕፅዋትና ቅመማ ቅመም አዘዋዋሪዎች፣ የታጠቁ ቡድኖችና ሌሎችም በውንብድና ላይ የተሠማሩ በተደጋጋሚ የሚጋጩባት ግዛት ነች። ይህ ዓመት ሜክሲኮ ውስጥ ለሚገኙ ጋዜጠኞች ግድያ የበዛበት ተደርጎ ሲመዘገብ ሜክሲኮ ከጦር ሜዳ ውጭ ለሪፖርተሮች አደገኛ የሆነች ሃገር መሆኗን በዘገባው አመልክቷል።
በጋዜጠኞች ግድያ ብዙ ጊዜ የሚነሱት የተደራጁ የወንጀል ቡድኖች ቢሆኑም ፖለቲከኞችም እንደሚጠረጠሩ ሪፖርቱ አክሎ ገልጿል።
ከዚህ በፊት በተፈፀሙ ግድያዎች የተወሰኑ ተጠርጣሪዎች የተያዙ ቢሆንም የተጠያቂነት አለመኖር በመስፋፋቱ የጋዜጠኞች ግድያ እየጨመረ መምጣቱን በሜክሲኮ የጋዜጠኞች ደኅንነት ተሟጋቹ ዓለምአቀፍ ቡድን /ሲፒጄ/ ወኪል የሆኑት አርጆን ሎፔዝ ገልፀዋል።