አስተዳደሩ በቻይና ኩባንያዎች ባለቤትነት በተያዙ፣ ወይም ቻይና ውስጥ በተፈበረኩ መርከቦች ላይ የተነጣጠረ ተጨማሪ የመቀጮ ክፍያ የሚጥል ሃሳብ ነው ያቀረበው። ይህም አሁን ያለውን ‘የዓለም ንግድ የኢኮኖሚዎች ይዞታ በእጅጉ ይቀይራል’ ሲል ቃል ገብቷል።
አዲሱ ፖሊሲ ሸቀጦችን ወደ ዩናይትድ ስቴትስ በሚያጓጉዙበት ወቅት፣ በበርካታ ወደቦች ለመቆም የሚገደዱት በቻይና የተያዙ እና ቻይና ውስጥ የተሰሩ የሶስተኛ ሀገር ይዞታ የሆኑ የጭነት መርከቦች፣ በእያንዳንዱ ወደብ በሚቆሙበት ወቅት የ1 ሚሊዮን ዶላር ወይም ከዚያ በላይ የሚሆን ክፍያ የሚጠይቅ እና በእያንዳንዱም ወደብ ተጨማሪ ክፍያ እንዲጠብቃቸው የሚያደርግ ነው።
‘ቻይና የአለም አቀፍ የመርከብ ግንባታ ኢንዱስትሪውን ኢፍትሃዊ በሆነ መልኩ አዛብታለች’ በሚል በርካታ የዩናይትድ ስቴትስ የሰራተኛ ማህበራት ካቀረቧቸው ክሶች ምርመራ ጋር በማያያዝ ነው፤ የዩናይትድ ስቴትስ የንግድ ጉዳዮች ተጠሪ ፅሕፈት ቤት፤ ባለፈው አርብ ይህን ዕቅዱን ይፋ ያደረገው።
በፕሬዚዳንት ጆ ባይደን አስተዳደር ወቅት በጉዳዩ ዙሪያ የተጀመረው ምርመራ ባለፈው ወር ነው ውጤቱ ይፋ የተደረገው። አስተዳደሩ እቅዱ ‘ተግባራዊ ይሁን ወይንስ ይቅር’ የሚለውን እስከሚወስንበት በአውሮፓውኑ የቀን አቆጣጠር እስከ ፊታችን መጋቢት 24 ባለው ጊዜ ለህዝብ አስተያየት ክፍት እንደሚደረግ ተገልጧል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የቻይና የውጭ ጉዳይ ሚንስቴር መሥሪያ ቤት ቃል አቀባይ ሊን ጂያን በትላንትናው ዕለት የዩናይትድ ስቴትስን እርምጃ ክፉኛ የተቹበትን አስተያየት ሰንዝረዋል።
መድረክ / ፎረም