በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ተመድ እና የረድኤት ድርጅቶች ወደ ሱዳን እንዲመለሱ ድንበር የለሹ የሐኪሞች ቡድን ጠየቀ


ከሴናር ግዛት የተፈናቀሉ ሱዳናውያን፣ በገዳረፍ ከተማ በአል-ሁሪ ወረዳ ሰፍረው እአአ ሃምሌ 14/2024
ከሴናር ግዛት የተፈናቀሉ ሱዳናውያን፣ በገዳረፍ ከተማ በአል-ሁሪ ወረዳ ሰፍረው እአአ ሃምሌ 14/2024

በተባበሩት መንግሥታት ሥር የሚገኙ እና ዓለም አቀፍ የርዳታ ድርጅቶች ወደ ሱዳን ተመልሠው ሕዝቡን መርዳት እንዲቀጥሉ፣ ድንበር የለሽ የሐኪሞች ቡድን (ኤም ኤስ ኤፍ) ጥሪ አድርጓል።

ድንበር የለሽ የሐኪሞች ቡድን ዓለም አቀፍ ፕሬዝደንት ክርስቶስ ክርስቱ ለኤ ኤፍ ፒ ዜና ወኪል እንደተናገሩት ፣ ለ15 ወራት በተደረገው ጦርነት አንድ ሦስተኛ የሚሆኑት ተጎጂዎች ሴቶችና ዕድሚያቸው ከ10 ዓመት በታች የሆኑ ሕፃናት ናቸው።

ፕሬዝዳንቱ አክለው፣ “ጦርነቱ በሃገሪቱ የነበረውን አብዛኛውን የርዳታ ሥራ እንዲቆም አስገድዷል። በርካታ ድርጅቶች ለጥንቃቄ በሚል የጦርነቱን አዝማሚያ ለማየት መጠበቅን መርጠዋል” ብለዋል።

የፕሬዝደንቱ ጥሪ የመጣው ሁለቱም የጦርነቱ ተሳታፊ ወኪሎች ጀኒቫ ላይ ውይይታቸውን በቀጠሉበት ወቅት ነው።

ረሃብ በተጋረጠበትና ጦርነቱ እንደሚቆም ፍንጭ በማይታይበት በዚህ ወቅት፣ ሌሎች ድርጅቶች በተለይም በተባበሩት መንግሥታት ሥር ያሉ ድርጅቶች ወደ ሃገሪቱ ተመልሰው ይበልጥ እንዲሠሩ ፕሬዝደንቱ ጥሪ አድርገዋል።

ለሱዳን የሚሰጠው የገንዘብ ርዳታ አነስተኛ በመሆኑ፣ በርካታ የርዳታ ቡድኖች የገንዘብ ችግር እንደገጠማቸውም ገልፀዋል።

በሱዳን ለርዳታ የተሠማሩ ቡድኖች ከሁለቱም ተፋላሚ ወገኖች ጥቃት የሚደርስባቸው ሲሆን፣ በዛች ሃገር የርዳታ ሥራ መሥራት የማይቻልበት ደረጃ ደርሷል ብለዋል።

መድረክ / ፎረም

XS
SM
MD
LG