በቱርክ ትናንት እሁድ በተካሄደው የአካባቢ ምርጫ ዋናው ተቃዋሚ ፓርቲ በዋና ዋና ከተሞች የበላይነትን አግኝቷል። የፕሬዝደንት ረሽፕ ታይፕ ኤርዶዋን ፓርቲ ከተሞችን መልሶ ለመቆጣጠር የነበረውን ዕቅድ ያጨናገፈ ድል ነው ተብሏል።
እስከ አሁን ዘጠና በመቶ የሚሆነው ድምፅ የተቆጠረ ሲሆን፣ የሪፐብሊካን ሕዝባዊ ፓርቲን የሚወክሉትና የኢኮኖሚ መዲና የሆነችው የኢስታንቡል ከንቲባ ኢክረም ኢማሞግሉ በከፍተኛ ድምፅ እየመሩ እንደሆነ መንግስታዊው የአናዶሉ ዜና አገልግሎት አስታውቋል።
የመዲናዋ አንካራ ከተማ ከንቲባ ማንሱር ያቫስ በሃያ አምስት ነጥብ ብልጫ በማሳየት ሥልጣናቸውን ማስጠበቅ ችለዋል።
ተቃዋሚው ፓርቲ፤ ከ81 ከተሞች ውስጥ፣ የኤርዶዋን ፓርቲ የሚቆጣጠራቸውን አንዳንድ ከተሞች ጨምሮ፣ 36 በሚሆኑት የበላይነትን ያገኘ ሲሆን፣ በመላ አገሪቱ ከተሰጠው ድምፅ 37 በመቶ አግኝቷል። የኤርዶዋን ፓርቲ ደግሞ 36 በመቶ እንዳገኘ የአናዱሎ ዘገባ አመልክቷል።
ከሃያ ዓመታት በላይ በሥልጣን ላይ የቆዩት ኤርዶዋን፣ በፓርቲያቸው ላይ የደረሰውን ሽንፈት ተቀብለው፣ ፓርቲው ሁኔታዎቹን በቅርብ እንደሚያጠና እና ግለሂስ እንደሚያደርግ አስታውቀዋል።
መድረክ / ፎረም