በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

የቻይና እና የአሜሪካ ከፍተኛ ባለስልጣናት ውይይት ውጥረት እንዳይባባስ ይረዳል ተባለ


ፋይል - የቻይና የንግድ ሚኒስትር ዌንታኦ ዋንግ
ፋይል - የቻይና የንግድ ሚኒስትር ዌንታኦ ዋንግ

በዚህ ሳምንት በዩናይትድ ስቴትስ ጉብኝት ያደረጉት የቻይና የንግድ ሚኒስትር ዌንታኦ ዋንግ ከአሜሪካ የንግድ ሚኒስትር ጂና ሬይማንዶ እና ከአሜሪካ የንግድ ወኪል ካትሪን ታይ ጋር ተገናኝተው ተወያይተዋል።

ስብሰባው የተካሄደው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን በንግድ እና በፀጥታ ጉዳዮች የሻከረው የሁለቱ ሀገሮች የሁለትዮሽ ግንኙነት መሻሻል ማሳየቱን ከአመላከቱ እና በየካቲት ወር የአሜሪካ ተዋጊ ጀት በአሜሪካ ግዛት ላይ ሲያንዣብብ የነበረ የቻይና የስለላ ፊኛን መቶ ከጣለ በኃላ ነው።

በዚህ ወር መጀመሪያ፣ የአሜሪካ ብሄራዊ የፀጥታ ጉዳዮች አማካሪ የሆኑት ጄክ ሱሊቫን ከቻይና የውጭ ፖሊሲ ባለስልጣን ዋንግ ዪ ጋር በቪየና ተገናኝተው በተነጋገሩበት ወቅት፣ አሜሪካ የስለላ ፊኛውን ጉዳይ ትታ ወደፊት መራመድ እንደምትፈልግ ተናግረው ነበር።


ውጥረቱን ለማርገብ በአሜሪካ የንግድ ሚኒስትር ጂና ሬይማንዶ እና በቻይና አቻቸው ዋንግ ዌንታኦ መካከል ሐሙስ እለት የተደረገውን፣ እንዲሁም አርብ እለት ከአሜሪካ የንግድ ወኪል ካትሪክ ታይ ጋር ያደረጉትን ውይይት ጨምሮ ሌሎች በከፍተኛ ባለስልጣናት መካከል ተጨማሪ ንግግሮችም እየተካሄዱ ነው።

በስቲምሰን ማዕከል የቻይና ፕሮግራም ዳይሬክተር ዩን ሰን በሰጡት አስተያየት፣ አሜሪካ ከቻይና ጋር፣ የሁለት ኃያላን ሀገራት ፉክክር ማድረግ እንደምትችል ከማሳየት እና የአየርን ንብረት ለውጥን መዋጋት እና ህገወጥ ዝውውሮችን ማስቆም በመሳሰሉ ጉዳዮች ላይ ትብብርን ከመፈለግ ባሻገር፣ ቤይጂንግ በዩክሬን ጦርነት ላይ ገንቢ ሚና እንዲኖራት ትፈልጋለች ብለዋል።

ቻይና በበኩሏ ለሀገሯ አሳሳቢ በሆኑት፣ አሜሪካ በግማሽ ኤሌክትሪክ አስተላላፊ በሆኑ ቴክኖሎጂዎች ላይ የጣለችው ገደብ የመሳሰሉ ጉዳዮች ዙሪያ ጥቅም ለማግኘት ፍላጎት እንዳላት ተዘግቧል።

XS
SM
MD
LG