በቡርኪናፋሶ በሚገኝ አንድ መንደር በተካሄደ የጅምላ ጭፍጨፋ ሴቶች እና ጨቅላ ህፃናትን ጨምሮ 136 ሰዎች መሞታቸውን ከጥቃቱ የተረፉ ነዋሪዎች አስታወቁ።
ነዋሪዎቹ ሚያዚያ 12 ቀን ለደረሰው ለዚህ ጥቃት፣ የሀገሪቱን የጸጥታ ኃይሎች ተጠያቂ አድርገዋል።
ባለፈው ሳምንት በካርማ ሰሜናዊ መንደር ውስጥ እና አካባቢው የቡርኪናፋሶ ታጣቂ ኃይሎችን ዩኒፎርም የለበሱ ሰዎች፣ ወደ 60 የሚጠጉ ንፁሃን ዜጎችን መግደላቸው ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ አቃቤ ህግ እልቂቱን በተመለከተ ምርመራ ጀምሯል።
ከአልቃይዳ እና እስላማዊ መንግስት ጋር ከተገናኙ ታጣቂዎች ጋር በምትዋጋው ሀገር ከደረሱት ጥቃቶች እጅግ የከፋው መሆኑ የተገለፀው ይህ የጅምላ ጭፍጨፋ በተባበሩት መንግስታት ሰብዓዊ መብት ተቋም ውግዘት የደርሰበት ሲሆን ምርመራ እንዲካሄድም ጥሪ ቀርቧል።
ቡርኪናፋሶ ካለፉት አስር አመታት ወዲህ ከጎረቤት ማሊ ከተስፋፋው ጥቃት አድራሽ እስላማዊ ፅንፈኛ ቡድን ጋር ከሚታገሉ በርካታ የምዕራብ አፍሪካ ሀገራት መካከል አንዷ ስትሆን፣ ቡድኑ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን ህይወት ሲያጠፋ ከ2 ሚሊየን በላይ የሚሆኑ ደግሞ አፈናቅሏል።
የሀገሪቱ ወታደራዊ መንግስት፣ ታጣቂዎቹ የተቆጣጠሩትን አካባቢ ለማስመለስ በሚል መጠነ ሰፊ ጥቃት እያካሄደ ይገኛል።