በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

የፍልስጤሙ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የጉዞ ፍቃዳቸው በእስራኤል መሰረዙን ተናገሩ



የፍልስጤም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ራይድ ማልኪ በዓለም አቀፉ የወንጀል ፍርድ ቤት በነበረ የፕሬስ ማስገንዘቢያ ላይ ንግግር አድርገዋል።
የፍልስጤም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ራይድ ማልኪ በዓለም አቀፉ የወንጀል ፍርድ ቤት በነበረ የፕሬስ ማስገንዘቢያ ላይ ንግግር አድርገዋል።

የፍልስጤም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እሰራኤል የጉዞ ፍቃዳቸውን እንደሰረዘችባቸው በዛሬው ዕለት አስታወቁ ። የአሁኑ እርምጃ የከረረ አቋም ያለው አዲሱ የእስራኤል መንግስት በፍልስጤማዊያን ላይ እንደሚተግብራቸው ከቀናት በፊት ያስታወቃቸው የቅጣት እርምጃዎች ክፍል ተደርጎ ተቆጥሯል።

ራይድ ማልኪ የብራዚል ፕሬዚደንትን በዓለ ሲመትን ተካፍለው ሲመለሱ እስራኤል የጉዞ ፍቃዳቸውን እንደሰረዘችባቸው እንደ ሰሙ ተናግረዋል። ይህ የጉዞ ፍቃድ የፍልስጤም ባለስልጣናት ከተቀረው ፍልስጤማዊ በተለየ መልኩ ፣ በእስራኤል ቁጥጥር ስር ባለችው ዌስት ባንክ በቀላሉ እንዲገቡ እና እንዲወጡ ያስችላቸዋል ።

የእስራኤል መንግስት ይሄን እርምጃ ያጸደቀው ፣ፍልስጤማዊያን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከፍተኛ የዳኝነት አካል እስራኤል የተቆጣጠረቻቸውን ቦታዎች በተመለከተ ሀሳቡን እንዲሰጥ ግፊት በማድረጋቸው ለመቅጣት መሆኑ ተዘግቧል ።

ይህ ውሳኔ የአሁኑ የእስራኤል መንግስት ስልጣን በያዘ በጥቂት ቀናት ውስጥ በፍልስጤማዊያን ላይ የያዘውን የከረረ አቋም የሚያሳይ ነው ተብሏል።

ዓለም አቀፍ ህጎችን በመጣስ ረገድ ልትቀጣ የሚገባት እስራኤል መሆኗን የተናገሩ ፍልስጤማዊያን የማልኪ የጉዞ ፍቃድ መሰረዙን አውግዘዋል። የእስራኤል ባለስልጣናት እስካሁን ማረጋገጫ አልሰጡም።

ጠቅላይ ሚኒስትር ቢኒጃሚን ኔትኒያሁ ዛሬ በነበረ የመንግስት ካቤኔ ስብሰባ ላይ እርምጃው በተባበሩት መንግስታት ዘንድ በታየው " መጠን ያለፈ-ጸረ-እስራኤላዊነት " ላይ ያነጣጠረ እንደሆነ ተናግረዋል ።

አርብ ዕለት የመንግስቱ የደህንነት መስሪያቤት 39 ሚሊየን ዶላር ለፍልስጤማዊያን አስተዳደር እንዳይገባ በማገድ በምትኩ ገንዘቡ በፍልስጤማዊያን ታጣቂዎች ቤተሰባቸው ላይ ጉዳት ለደረሰባቸው እስራኤላዊያን ካሳ እንዲከፈል መወሰኑ ይታወሳል ። ዘገባው የአሶሼትድ ፕረስ ነው።

XS
SM
MD
LG