ለመጀመሪያ ግዜ የተላከው የኢቦላ ክትባት ትላንት ሐሙስ ኡጋንዳ ሲደርስ አገሪቱ እንደ አዲስ ያገረሸውን ስርጭት ለመቆጣጠር ተስፋ አድርጋለች።
“የሱዳን ኢቦላ” ለሚባለው የኢቦላ ዓይነት የሚያገለግለውን 1ሺህ 200 የሙከራ ክትባቶች የኡጋንዳ ጤና ጥበቃ ሚኒስትር ጄን ሩት አሰንግ ተረክበዋል።
ኡጋንዳ ኢቦላ በአገሪቱ መከሰቱን ያስታወቀችው ባለፈው መስከረም ሲሆን እስከ አሁን 56 ሰዎች ሲሞቱ 140 ሰዎች ደግሞ በተውሳኩ ተይዘዋል።
ላለፉት 9 ቀናትአዲስ የተያዙ ሰዎች አለመኖራቸውን ሚኒስትሯ አስታውቀው፣ ቁጥጥሩ እስከ ጥር 2 ይቀጥልና፣ ከዛ ቀን በኋላ በዓለም የጤና ድርጅት አጋዥነት አገሪቱ ከበሽታው ነጻ ትሆናለች ብለው ተስፋ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል።
በመጀመሪያው ዙር የገባው ክትባት በበሽታው ከታያዙ ጋር ንክኪ ለነበራቸው እንዲሁም በከፍተኛ ደረጃ ለበሽታው ተጋላጭ ለሆኑ ሰዎች እንደሚሰጥ የአሶስዬትድ ፕረስ ዘገባ አመልክቷል: