ባለፉት ሦስት ወራት ወደ ትግራይ ክልል የገባ የእርዳታ እህል የጫነ መኪና እንደሌለ የክልሉ የውጭ ግንኙነት ጽ/ቤት ገለፀ።
ባለፉት ስምንት ወራት ከ24 ሺሕ በላይ የእርዳታ እህል የጫኑ መኪኖች ወደ ትግራይ ክልል መግባት ሲገባቸው የገቡት ግን 1,393 ብቻ መሆናቸውን የጽሕፈት ቤቱ ከፍተኛ አመራር የሆኑትን ፕሮፌሰር ክንደያ ገብረህይወት ለአሜሪካ ድምፅ ተናግረዋል።
የኮምዩኒኬሽንስ ሚኒስትር ደ’ኤታ አቶ ከበደ ዴሲሳ ለቪኦኤ በሰጡት ምላሽ “ውንጀላው ሐሰት ነው” ብለዋል፡፡
“ህወሓት በአፋር በኩል በቅርቡ ጥቃት የከፈተው የእርዳታ መስመሩ እንዲዘጋ በማሰብ ነው” ያሉት አቶ ከበደ ዓላማውም በሱዳን መስመር እንዲከፈት ጫና ለማሳደር እንዲሁም “ሊከፍት አስቧል” ላሉት አዲስ ወረራ የክልሉን ሕዝብ ለማሰለፍ መሆኑን በመግለፅ ምላሽ ሰጥተዋል።