ዋሺንግተን ዲሲ —
ፈረንሳይ ለሱዳን አንድ ነጥብ አምስት ቢሊዮን ዶላር በብድር ልትሰጥ ማቀዷን ዛሬ አስታወቀች።
ገንዘቡ ሱዳን ለዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅት መክፈል ያለባትን ዕዳ ለመክፈል የሚረዳ መሆኑ ታውቋል።
የፈረንሳይ የገንዘብ ሚኒስትር ብሩን ለ ሜይር ለሱዳን ብድሩን እንዲሚሰጥ ዛሬ የፈረንሳዩ ፕሬዚደንት ኢማኑኤል ማክሮን በሚያስተናግዱት የሱዳን እርዳታ ዓለም አቀፍ ጉባኤ መክፈቻ ላይ ይፋ አድርገዋል።
ገንዘቡ ሱዳን ያለባትን የሃምሳ ቢሊዮን ዶላር የውጭ ዕዳ እንድትከፍል እና ኢኮኖሚዋን መልሶ ለመገንባት የውጭ መዋእለ ነዋይ መሳብ እንድትችል ለመርዳት የታቀደ መሆኑ ተመልክቷል።