በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ፒስ ኮር - የሰላም ጓድ የበጎ ፈቃደኞች ድርጅት 60 አመት ሞላው


ፒስ ኮር - የሰላም ጓድ የበጎ ፈቃደኞች ድርጅት 60 አመት ሞላው
please wait

No media source currently available

0:00 0:05:27 0:00

የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት የነበሩት ጆን ኤፍ ኬኔዲ ሰላምና አብሮነትን ለማስፋፋት ዓለም አቀፍ የበጎ ፈቃደኞች ድርጅት የሆነው የሰላም ጓድ (ፒስ ኮር) እንዲቋቋም ፊማቸውን ካኖሩ 60 አመታት ተቆጠሩ።

ፒስ ኮር ተብሎ የሚጠራው የሰላም ጓድ አላማ የተጠነሰሰው የዛሬ 60 አመት፣ የቀድሞው ፕሬዝዳንት ጆን ኤፍ ኬኔዲ ወጣት አሜሪካኖች የተለያዩ አገራት በመሄድ ከሌሎች ዜጎች ጋር አብሮ በመስራት እንዲማሩ እቅድ ባወጡበት ወቅት ነው።

"ልዩ የሚያደርገው ነገር የሰላም ጓድ አባል በመሆን የሚገኝ የድሞዝ ክፍያ አለመኖሩ ነው። ወደ ሌሎች ሀገራት ሄደው ህዝቡ እንደሚኖረው ሆነው ይኖራሉ። ሁለት ወይም ሶስት አመታት በመቆየት ራሳቸውን ለሰላምና በዓለም ዙሪያ ያሉ ሰዎችን አንድ በሚያደርጋቸው ጉዳዮች ሰጥተው ይሰራሉ።"

ይህ የፕሬዝዳንቱ እቅድ በወቅቱ ስጋቶች የነበሩበት ቢሆንም፣ አሁን ስልሳ አመታትን ማስቆጠር ችሏል። የጆን ኦፍ ኬኔዲ ላይብረሪና ሙዚየም ዳይሬክተር የሆኑት አላን ፕራይስ፣ የተጀመረበት አላማ ግቡን መቷል ይላሉ።

"እጅግ በጣም ግሩም ሀሳብ ነበር። ጠንክረው ለሰሩት በጎ ፈቃደኖችና እነሱን ላስተናገዱት ሀገሮች ምስጋና ይግባቸውና፣ በረጅም ግዜ ይሳካል ተብሎ የታቀደው ሰላምንና አብሮነትን የማሳደግ እቅድ በአብዛኛው የተሳካ ነበር።"

ባለፍት 60 አመታት ከ241 ሺህ የሚበልጡ፣ በየትኛውም የእድሜ ክልል የሚገኙ የሰላም ጓድ በጎ ፈቃደኞች በዓለም ዙሪያ በሚገኙ 140 ሀገራት ማገልገላቸውን የድርጅቱ ተጠባባቂ ዳይሬክተር ካሮል ስፓን ይናገራሉ።

"በሰላም ጓድ በጎ ፈቃደኛ ሆነው የሚሳተፉ ሰዎች እድሜያቸው ከ20 እስከ 85 ይሆናል። በርግጥ ብዙዎቹ በ 20ዎቹ እድሜ ውስጥ ናቸው ግን እኔ በማላዊ የድርጅቱ ተጠሪ ሆኜ ባገለገልኩበት ወቅት የ82 አመት ሴት በጎ ፈቃደኛ ሆነው ያገለግሉ ነበር። በስራቸውም እጅግ የሚያስደንቁ ነበሩ።"

ስፓን እራሳቸው የሰላም ጓድ አባል ሆነው በሮማንያ ለማገልገል ሲወስኑ ገና የ26 አመት ወጣት ነበሩ። ወቅቱ የኮሚዩኒዝም ስርዓት ከወደቀ ከሶስት አመት በኃላ እንደነበር የሚያስታውሱት ስፓን አንዳንድ ሰዎች በጥርጣሬ ቢያዋቸውም ለሳቸው ህይወትን የሚቀይር ልምድ የቀሰሙበት እንደነበር ያስታውሳሉ።

"ብዙ ጊዜ በጎ ፈቃደኛ ሆነው ወደ ሰላም ጓድ የሚመጡ ሰዎች በህይወትና በአኗኗር ላይ የራሳቸው የሆነ አመለካከትና ተስፋ ኖሯቸው ነው። ከዛ ከነሱ የተለየ ልምድና አኗኗር ካላቸው ሰዎች ጋር መኖርና መስራት ሲጅምሩ ጥያቄዎች መጠየቅ ይጀምራሉ። ነገሮችን የበለጠ ለማወቅ በሞከሩ ቁጥር ደግሞ ከጀርባ ያለውን፣ ነገሮች ለምን ከራሳቸው ሀገር የተለየ እንደሆኑና ሰዎች ለምን የራሳቸው እሴቶችና ታሪኮች እንዳሏቸው ይረዳሉ።"

ድዌይን ማቲዮስ እ.ኤ.አ ከ2013 እስከ 2015 ዓ.ም በማላዊ አገልግሎ የተመለሰ በጎ ፈቃደኛ ነው። በአሁኑ ወቅት በቤቶችና ከተማ ልማት ውስጥ እየሰራ ዋሽንግተን በሚገኘው ሀዋርድ ዩንቨርስቲ የዶክትሬት ዲግሪውን ለማግኘት ይማራል። በአርካንሳስ ግዛት ተወልዶ ያደገው ማቲዮስ ከፒስ ኮርፕስ ጉዞው በፊት የትም ጉዞ አርጎ እንደማያውቅ ይናገራል።

"ማላዊ ምንም ያልጠበኩት ነገር ነው የገጠመኝ። በተለይ የመጀመሪያው ሳምንት ለኔ እጅግ አስፈሪ ነበር። ነገር ግን መጨረሻ ላይ ወደ ሀገሬ ልመለስ ስል አልቅሻለሁ። መመለስ አልፈለኩም ነበር። እስካሁን በህይወቴ ከወሰንኳቸው ውሳኔዎች በጣም የምደሰትበት ጉዞ ነው።"

ማቲዮስ ማላዊ በነበረበት ጊዜ የማህበረሰቡ የጤና አማካሪ ሆኖ በተልያዩ ፕሮጀክቶች ላይ አገልግሏል። በተለይ በጣም የሚኮራበት ስራው የወጣቶች ማዕከል ለማቋቋም ማህበረሰቡን አስተባብሮ የ7ሺህ ዶላር በጀት ማግኘት መቻሉ እንደነበር ያስታውሳል።

"ማህበረሰቡ ከሚፈለገው በጀት 30 በመቶ የሚሆነውና መሬት አዋጣ። የሰው ጉልበትና የሸክላ ጡብ የመሳሰሉትም እንዲሁ የማህበረሰቡ ነው። ፕሮጀክቱ ቀጣይነት እንደሚኖረው እርግጠኛ የነበርነው ለዛ ነው ምክንያቱም ማህበረሰቡ ፈልጎት የተሳተፈበት ነበር።"

ሌላው ክሪስ ደስቲሽ ከ2018 እስከ 2020 በጉዋታላማ አገልግሏል። አሁን ደግሞ በሰላም ጓድ የበጎ ፈቃደኞች ምልመላ ስራ ይሰራል።

"ማያን በተሰኘች ትንሽ መንደር ውስጥ ነው የኖርኩት። በመንደሯ ምናልባት 2000 ሰዎች ቢኖሩ ነው። ሶስት ትውልድ የቤተሰብ አባላት ባሉበት ቤት ውስጥ ነው የኖርኩት። ግርግር ቢበዛም ግን በጣም ደስ የሚልና የሚወደድ ቤተሰብ ነበር።"

ደስቲሽ በቆይታው በጉዋታማላ የግብራና ሚኒስትር፣ የገጠር ማስፋፊያ ፕሮግራም የማስፈፀም ስራ ይሰራ ነበር።

"በዋናነት ለማያን ገበሬዎች የአቅም ግንባታ ስልጠና እሰጥ ነበር። አላማውም ምግብ የማብቀል አቅማቸውን ለመገንባት፣ በአካባቢው የሚያጋጥመውን የምግብ አቅርቦት እጥረት ለመቅረፍና ረሀብን ለማጥፋት ነው። "

ማቲዎስም ሆነ ደስቲሽ የሰላም ጓድ በማገልግለአቸው ከሌላ ከየትም ማግኘት የማይችሉትን በርካታ የህይወት ትምህርቶችንና ጥበቦችን ማግኘት እንደቻሉ ይመሰክራሉ።
XS
SM
MD
LG