የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ለ“አዲስ አበባ” ውዝግብ ምላሽ ሰጠ

  • ቪኦኤ ዜና

የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት

በኢትዮጵያ የአሜሪካ ኤምባሲ በቅርቡ በኤክስና በፌስቡክ በኦሮምኛ ባወጣው የሥራ ማስታወቂያ ላይ አዲስ አበባን “ፊንፊኔ” ከማለቱ ጋር የተያያዙ ደብዳቤዎች እንደደረሱት የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ዛሬ አስታወቀ።

የመሥሪያ ቤቱ ቃል አቀባይ ቪኦኤ ላቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ ኢትዮጵያ ያለው የዩናይትድ ስቴትስ ኤምባሲ ቋንቋን በሚመለከት የሃገሪቱን ህገመንግሥትና ህግጋት እንደሚያከብር ገልፀዋል።

ቃል አቀባዩ አክለውም “ኤምባሲው የቆንስላ አገልግሎቶቹና የዲፕሎማሲ መርኃግብሩ በተቻለ መጠን ስፋት ላለው ኢትዮጵያዊ ተመልካችና አድማጭ እንዲደርስ ለማድረግ በመላ ዓለም እንደምናደርገው ሁሉ መደበኛና ዲጂታል ሚድያን ዘወትር ይጠቀማል” ብለዋል።

SEE ALSO: የአሜሪካ ኤምባሲ ዐዲስ አበባን በቁቤ “ፊንፊኔ” ማለቱ ተቃውሞ ሲያስነሣ ያበረታቱም አሉ

የዚህ ጥረት አካል በሆነ እንቅስቃሴ ኤምባሲው ለኢትዮጵያዊያን የሚሰጠውን የቆንስላ አገልግሎት በስፋት ለማስተዋወቅ ያስችላሉ ባላቸው ቋንቋዎች ኅዳር 12 ዘመቻ መጀመሩን ቃል አቀባዩ አመልክቷል።

ቪድዮዎች በእንግሊዝኛ፣ በአማርኛ፣ በኦሮምኛ፣ በትግርኛና በሶማሊኛ መሠራታቸውንም ጠቅሰዋል።

ይህንኑ የሚመለከቱ ደብዳቤዎች እንደደረሷቸው የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤቱ ቃል አቀባይ ጠቁመው በተለመዱት የዲፕሎማሲ አሠራሮች እየተስተናገዱ መሆናቸውን አስታውቀዋል።