“እስራኤል ቀጠናውን ወደ የለየለት ጦርነት እየገፋች ነው” የአካባቢው ሃገራት

  • ቪኦኤ ዜና

በሰሜናዊ ጋዛ ሰርጥ ጃባሊያ ውስጥ በእስራኤል እና ሃማስ ግጭት የተፈናቀሉ ሰዎች መጠለያ ስፈር ውስጥ ከባድ ጉዳት የደረሰባቸው ሕንፃዎች

በቀጠናው አደገኛ በሆነ ሁኔታ ጦርነቱ ከመስፋፋቱ በፊት፣ “እስራኤል በጋዛ ላይ የምትፈጽመው ጥቃት” እንዲቆም ግብፅ፣ ዮርዳኖስ እና ኢራቅ ዛሬ ረቡዕ በጋራ ባወጡት መግለጫ አስታውቀዋል።

የሶስቱ ሃገራት የውጪ ጉዳይ ምኒስትሮች ባወጡት መግለጫ፣ እስራኤል በሌባኖስ ላይ የምትወስደውን ወታደራዊ እርምጃ አውግዘው፣ “እስራኤል ቀጠናውን ወደ የለየለት ጦርነት እየገፋች ነው” ብለዋል።

ምኒስትሮቹ በተጨማሪም፣ የተመድ የፀጥታው ም/ቤት እና ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ጦርነቱን ለማስቆም እንዲንቀሳቀሱ ጠይቀዋል።

SEE ALSO: እስራኤል በሊባኖስ ላይ ያካሄደችው ጥቃት ቀጠናዊ ጦርነት ሊቀሰቀስ ይችላል የሚል ስጋት ፈጥሯል

በሰሜን እስራኤል ሄዝቦላ ለአንድ ዓመት ያህል በሮኬት በፈጸመው ጥቃት ሳቢያ የተፈናቀሉ ዜጎችን ወደ መኖሪያቸው ለመመለስ በሚል፣ እስራኤል በሌባኖስ በሚገኘው ሄዝቦላ ላይ ጥቃቷን አጠናክራ ሰንብታለች፡፡

እስራኤል በምድርና በአየር በጋዛ ላይ በምታደርሰው ጥቃት ቢያንስ 41ሺሕ 495 ፍልስጤማውያን እንደሞቱ እና ከ96 ሺሕ በላይ ደግሞ ጉዳት እንደደረሰባቸው በጋዛ የሚገኘው የጤና ሚኒስቴር አስታውቋል።

ሐማስ ትላንት ማክሰኞ ባወጣው መግለጫ ደግሞ፣ በጋዛ ያለውን ጦርነት ለማስቆም የተባበሩት መንግስታት ድርጅት “አስቸኳይ እርምጃ” ይወስዳል ብሎ እንደሚጠብቅ አስታውቋል።