ዞን ዘጠኝ ለሽልማት ተመረጡ

የዞን ዘጠኝ ፀሐፊዎች የዓለም አቀፍ የፕሬስ ነፃነት ተሸላሚ እንዲሆኑ ተመርጠዋል፡፡

ዞን ዘጠኝ የ2015 ዓ.ም /በአውሮፓ አቆጣጠር/ የመናገር ነፃነት ተሸላሚ ሆኑ

Your browser doesn’t support HTML5

ዞን ዘጠኝ ለፕሬስ ነፃነት ሽልማት ተመረጡ

ዋና ፅሕፈት ቤቱ ኒው ዮርክ የሚገኘው በእግሊዝኛ መጠሪያው Committee to Protect Journalists ወይም ከስሙ ምኅፃር ሲፒጄ እየተባለ የሚታወቀው ዓለምአቀፉ የጋዜጠኞች ደኅንነት ተሟጋች ድርጅት ሃሣብን የመግለፅ ነፃነት እንዲጠናከር ስላበረከቱት አስተዋፅዖ የዞን ዘጠኝ ፀሐፊዎችን ሸልሟል፡፡

ሲፒጄ ዞን ዘጠኞችን ለሽልማት ማብቃቱን ያሳወቀው የመገናኛ ብዙኃን ነፃነት የዘንድሮ ተመራጮቹን ይፋ ሲያደርግ ሲሆን ዞን 9ኞችን ያጫቸው የመናገር ነጻነት በኢንተርኔት እንዲስፋፋ ላበረከቱት አስተዋፅዖ ነው።

የዞን ዘጠኝ ፀሀፊዎች በዌብ ሳይታቸው ሕገመንግሥታዊ መብቶች እንዲከበሩ የሚሟገቱ ሲሆን በፀረ-ሽብ ሕጉ ህዝብን በማነሳሳት በኢትዮጵያ መንግሥት ክሥ ተመሥርቶባቸዋል፡፡

ሁለቱ ፀሀፊዎች በፍትህ ምኒስቴር ክሳቸው ተቋርጦ የተፈቱ ሲሆን አራቱ አሁንም ታስረው ሦስቱ ስደት ላይ ይገኛሉ።

የዞን ዘጠኝ ጋዜጠኞችና የኢንተርኔት ፀሐፊዎች

ዓለም አቀፉ የጋዜጠኞች ደኅንነት ተሟጋች ቡድን - ሲፒጄ ለእነዚህ ወጣት የኢንተርኔት የመናገር ነፃነት ተሟጋቾች ከሌሎች ሦስት ጋዜጠኞች ጋር ዓለም አቀፉን ሽልማት የሰጠው መረጃ ለማድረስ በሙያቸው በጀግንነት ስላበረከቱት አስተዋፅዖ ነው።

የስፒጄ የአፍሪካ ፕሮግራም አስተባባሪ ሱ ቫለንታይን ለቪኦኤ በሰጡት ቃል “ሽልማቱ ለዞን ዘጠኝ ፀሐፊዎች ሥራ ዕውቅና ይሰጣል፤ በአፍሪካ በማኅበረሰብ መገናኛ ብዙኃንና በዌብ ሳይቶች አማካይነት የመናገር ነፃነትን ለማስፋፋት የሚጫወቱትን ቁልፍ ሚና ያጎላል፤ በየሀገሮቹ ያሉ መረጃዎችን ለህዝብ ለማድረስ ዌብ ሳይቶች ያላቸውን ድርሻ ያሳያል” ብለዋል፡፡

ከዞን ዘጠኝ በተጨማሪ ማሌዢያዊ የስላቅ ሰዓሊ ዙናር፣ ፓራጓያዊው ጋዜጠኛ ካንዲዶ ፊሁረዶ ሩዪዝ፣ ሶሪያዊው ቡድን ራቃ የዘንድሮው ሃሣብን የመግለፅ ነፃነት ተሸላሚዎች ሆነዋል።

ሁሉም በዓለም ዙሪያ መረጃ የማግኘት ነፃነት፣ ሃሣብን የመግለፅ ነፃነት፣ የመገናኛ ብዙኃን ነፃነት እንዲከበር የሚሠሩ ባለሙያዎች መሆናቸውን ሲፒጄ አመልክቷል።