በአማራ ክልል የመሬት መንሸራተት 19 ሰዎችን ገደለ

አከታትሎ የጣለ ዝናብ ያደረሰው የጎርፍ አደጋ በሀብሩ 2ሽህ ሰዎችን አፈናቅሏል

አቶ አሰፋ ነጋሲ በሀብሩ ወረዳ በመርሳ ከተማ ለረጂም ጊዜ የኖሩ የአገር ሽማግሌ ናቸው። አበይ ተራራ በሚባለው ስፍራ ከሰሩት ቤታቸው ቁልቁል ከተማዋን እየተመለከቱ የህዝቡ ብዛት ከጥቂት ሽዎች ወደ አስር ሽዎች ሲያድግ ተመልከተዋል።

በግብርና ስራ የተሰማሩት አቶ አሰፋ ቤት እሁድ ሌሊት በመሬት መንሸራተት ፈርሷል። አቶ አሰፋ ምሽቱን አነስ ባለች ቤት ስላሳለፉ በአደጋው ጉዳት አልደረሰባቸውም።

በዋናው ቤት ውስጥ የነበሩት ባለቤታቸው፣ ልጃቸውና የልጅ ልጃቸው ገበሬያቸውን ጨምረው ህይወታቸው አልፏል።

የድረሱን ጥሪ “እሪታውን” ጎረቤቶች ሲያሰሙ፤ የአካባቢው ሰውና ወዳጅ ዘመዶች ለእርዳታ ወደ አቶ አሰፋ ቤት ፍርስራሽ የተቀበሩ ሰዎችን ሊያድኑ ያመራሉ።

በዚህ ጊዜ ነው ትልቁና ብዙዎችን የጎዳው መንሸራተት የደረሰው። “እንደ ደማሚት መሬቱ ተገምሶ እላያችን ላይ ወደቀ ሲሉ” ከአደጋው የተረፉ ሰዎች ተናግረዋል።

የመሬት መንሸራተቱ 14 ሰዎችን ሲገድል ከ24 ያላነሱ ሰዎች ላይ የመቁሰል አደጋ አስከትሏል።

“ጉዳት የደረሰባቸው ሰዎች በወልዲያ ሆስፒታልና በመርሳ ጤና ጣቢያ በመታከም ላይ ይገኛሉ” ሲሉ የመርሳ ከተማ አስተደደር ባለስልጣን አቶ ሙሀመድ ያሲን ተናግረዋል።

“በአካባቢው የጎርፍ አደጋም ደርሷል… በተለይ በቡሆሮና በውርጌሳ አካባቢ ባለው ተደምሮ ከሁለት ሽህ በላይ ህዝብ የተፈናቀለ መሆኑን ነው መረጃው የሚያሳየው።” ብለዋል አቶ ሙሀመድ።

የህብሩ ወረዳ በግብርናና ከብት እርባታ የሚተዳደር አካባቢ ነው።

በጎርፉ ለተጎዱ ገበሬዎች የእርዳታ አቅርቦትና የመልሶ ማቋቋም ስራን ለማስተባበር እየጣረ መሆኑን የአካባቢው አስተዳደር ይናገራል።

በወረዳው ከዚህ በፊት እንዲህ ያለ ችግር ደርሶ ስለማያውቅ አቅርቦት ለማዳረስ የሚያስችሉ መሰረቶችና ልምዶች የሉም። ይሄም የእርዳታ አቅርቦቱን ሊያጓትተው ይችላል በሚል ስጋት አለ። የአካባቢው አስተዳደር ግን በቀጣይነት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና ተጎጂዎችን መልሶ ማቋቋም እንቅስቃሴ መጀመሩን አስታውቋል።