ለኮቪድ-19 መጋለጣቸው የተነገረውና የበሽታው ቀላል ምልክቶች እንደሚታዩባቸው የተገለፀው የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን ደኅና መሆናቸውንና ሥራቸውን እያከናወኑ መሆናቸውን ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት በቴሌቪዥን በተላለፈ መልዕክት ገልፀዋል።
“ደኅና ነኝ፣ ስለጭንቀታችሁ አመሠግናለሁ፤ ሥራዬን እያከናወንኩ ነኝ” ብለዋል ባይደን ባስተላለፉት አጭር መልዕክት።
Folks, I%27m doing great. Thanks for your concern. Just called Senator Casey, Congressman Cartwright, and Mayor Cognetti (and my Scranton cousins!) to send my regrets for missing our event today.Keeping busy! pic.twitter.com/uf7AsOg571
— President Biden (@POTUS) July 21, 2022
ዋይት ሃውስ ውስጥ አሁን እየተሰጠ ባለ ጋዜጣዊ መግለጫ የቤተ መንግሥቱ ቃል አቀባይ ካሪን ዣን-ፒየር ስለፕሬዚዳንቱ ጤንነት ለጋዜጠኞች ሲናገሩ ሃኪሞቻቸው ዛሬ ተከታታይ ምርመራ ሲያደርጉ ለሳርስ-ኮቭ2 ቫይረስ መጋለጣቸውን ማስተዋላቸውንና በኋላም አከታትለው ባደረጉት ምርመራ ማረጋገጣቸውን የሚገልፀውን መግለጫ በንባብ አሰምተዋል።
የዋይት ሃውስ የኮሮናቫይረስ ምላሽ አስተባባሪ ዶ/ር አሺሽ ዣ ከፕሬዚዳንቱና ከሃኪማቸውም ጋር መነጋገራቸውን፣ ፕሬዚዳንቱ ሙሉውን ክትባትና ሁለት ማጠናከሪያዎችን መውሰዳቸውን፣ የሰውነታቸው በሽታን የመቋቋም ሁኔታ አስተማማኝ መሆኑን፣ የሚስተዋሉባቸው እንደ ደረቅ ሳል፣ ቀላል መናፈጥና የድካም ስሜትን የመሳሰሉ “ቀላል” ያሏቸው ምልክቶች መሆናቸውን አመልክተዋል።
የዩናይትድ ስቴትስ የበሽታዎች መቆጣጠሪያና መከላከያ ማዕከላት /ሲዲሲ/ መመሪያ በሚያዝዘው መሠረት ፕሬዚዳንቱ ቤተመንግሥቱ ውስጥ ትነጥለው እንደሚገኙና ሁሉንም ሥራዎቻቸውን በተሟላ መልኩ እየተወጡ እንደሚቆዩ ዶ/ር ዣ ጠቁመው የፓክስሎቪድ ህክምና መጀመራቸውን ገልፀዋል።
ፕሬዚዳንቱ “እጅግ በጣም ጥሩ ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ፣ ትናንትም ማሳቹሴትስ ውስጥ እጅግ ከፍተኛ በሆነ ሙቀት ለግማሽ ሰዓት ያህል በጥሩ ሁኔታ ንግግር ማድረጋቸውን” ቃል አቀባይዋ አስታውሰዋል።
ባለቤታቸው ዶ/ር ጂል ባይደን ከቫይረሱ ነፃ መሆናቸው መረጋገጡንና ለዛሬ በተያዙ ዕቅዶች መሠረት ሥራዎቻቸውን እያከናወኑ መሆናቸውንም ቃል አቀባይዋ ዣን ፒየር ተናገረዋል።
ፕሬዚዳንት ባይደን 79 ዓመታቸው ነው።