በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

የፑቲን የመያዣ ትዕዛዝን በተመለከተ ደቡብ አፍሪካ የሕግ አማራጮቿን እያየች ነው


የፑቲን የመያዣ ትዕዛዝን በተመለከተ ደቡብ አፍሪካ የሕግ አማራጮቿን እያየች ነው
please wait

No media source currently available

0:00 0:01:31 0:00

ብሪክስ በመባል የሚታወቁ በኢኮኖሚ በመበልጸግ ላይ ያሉ አገራት ቡድን፣ በመጪው ነሐሴ በደቡብ አፍሪካ በሚያደርገው ስብሰባ ላይ፣ የጦር ወንጀል ፈጽመዋል በሚል የመያዣ ትዕዛዝ የወጣባቸው ቭላድሚር ፑቲን የሚገኙ ከሆነ ደቡብ አፍሪካ በማውጠንጠን ያላትን ህጋዊ አማራጮች ላይ ነች፡፡

ሩሲያ በዩክሬን ላይ ከፈጸመችው ወረራ ጋር በተያያዘ፣ ዓለም አቀፉ የወንጀል ችሎት በሩሲያው ፕሬዝደንት ቭላድሚር ፑቲን ላይ የመያዣ ትዕዛዝ አውጥቷል። የዓለም አቀፉ የወንጅል ችሎት ዓባል የሆነችው ደቡብ አፍሪካ፣ ፕሬዝደንት ፑቲን በአገሪቱ በሚካሄደው ስብሰባ ላይ የሚገኙ ከሆነ ይዛ ማስረከብ ይጠበቅባታል።

“ጉዳዩን በተመለከተ ያሉትን ሕጋዊ አማራጮች መንግስታችን በመመልከት ላይ ነው። እንዳልኩት አንድ ውሳኔ ላይ ከደረስን በኋላ፣ በጉዳዩ ላይ መናገር የሚገባቸው ፕሬዝደንቱ ናቸው” ብለዋል ከብሪክስ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትሮች ስብሰባ ጎን ለጎን ከዜና ሰዎች ጋር የተነጋገሩት የደቡብ አፍሪካው የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ናለዲ ፓንዶር።

ጆሃንስበርግ ውስጥ በነሐሴ ወር ሊደረግ ለታቀደው ስብሰባ፣ የብሪክስ አባላት ለሆኑት ብራዚል፣ ሩሲያ፣ ህንድ፣ ቻይና እና ደቡብ አፍሪካ ግብዣው ደርሷቸዋል።

በሩሲያ ከተያዙት የዩክሬን ግዛቶች ሕጻናትን አስገድደው አስወጥተዋል በሚል፣ ዓለም አቀፉ የወንጀል ችሎት በፕሬዝደንት ፑቲን ላይ ባለፈው መጋቢት የመያዣ ትዕዛዝ አውጥቷል። መስኮብ ክሱን ታስተባብላለች፡፡

በደቡብ አፍሪካ ባለሥልጣናት ዘንድ ትኩረት ያገኘው አንድ አማራጭ፣ ከዚህ በፊት የቡድኑ ሊቀመንበር የነብረችው ቻይና ስብሰባውን እንድታስተናግድ መጠየቅ ነው።

ስብሰባው ወደ ቻይና ተዛውሯል የሚለውን ወሬ ሃሰት ነው ሲሉ የሩሲያ ምክትል የውጪ ጉዳይ ሚኒትር የሆኑት ሰርጌይ ርያብኮቭ ባለፈው ሐሙስ ተናግረዋል።

የደቡብ አፍሪካው የቀድሞ ፕሬዝደንት ታቦ ምቤኪ፣ ስብሰባው ደቡብ አፍሪካ ውስጥ የመካሄዱ ነገር የሚሆን እንደማይመስላቸው ባለፈው ወር ተናግረው ነበር። “ሕጋዊ ግዴታ ስላለብን ፑቲንን ይዘን ማስረከብ አለብን፣ ግን ያንን ማድረግ አንችልም” ሲሉ ተደምጠዋል።

ደቡብ አፍሪካ፣ በስብሰባው ላይ ለሚታደሙ መሪዎች ዲፖሎማሲያዊ ያለመከሰስ መብት ሰኞ ዕለት ሰጥታለች፡፡ ይህ ግን በደቡብ አፍሪካ ለሚካሄዱ ማናቸው ዓለም አቀፍ ስብሰባዎች በተለምዶ የሚደረግ ነው ተብሏል። ያለመክሰስ መብቱ በዓለም አቀፍ ወንጀል ችሎት የሚወጡ መያዣ ትዕዛዞች ላይ የበላይነት የለውም ተብሏል።

የመያዣ ተዕዛዝ ወጥቶባቸው የነበሩት የቀድሞው የሱዳን ፕሬዝደንት ኦማር አልበሽረን ይዛ አላስረከበችም የሚል ወቀሳ ከስምንት ዓመታት በፊት ከደረሰባት በኋላ፣ ደቡብ አፍሪካ የዓለም ዓቀፍ ፍ/ቤቱን አባልነት ለመተው መከጀሏን ምልክት አሳይታ ነበር።

ገዢው የአፍሪካ ብሔራዊ ኮንግረስ ግን፣ በፍርድ ቤቱ የውስጥ አሰራር ውስጥ ለውጥ በማምጣት መሞከር ይሻላል በሚል ሃሳቡን አስቀርቶታል።

XS
SM
MD
LG