በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

በናይጄሪያ የከፋ የአልሚ ምግብ እጥረት ሕፃናትን እየጎዳ ነው


በናይጄሪያ የከፋ የአልሚ ምግብ እጥረት ሕፃናትን እየጎዳ ነው
please wait

No media source currently available

0:00 0:02:54 0:00

በዓለም አቀፍ ርዳታ ውስንነት ምክንያት፣ በሰሜን ምሥራቅ ናይጄሪያ፣ አራት ሚሊዮን ሰዎች ከፍተኛ የምግብ እጥረት እንደሚገጥማቸው፣ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አስታውቋል።

የተመድ የሰብአዊ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ቢሮ(OCHA)፣ ጋዜጠኞችን ወደ አካባቢው በመውሰድ፣ የችግሩ አስከፊነት ያለበትን ደረጃ እንዲታዘቡ አድርጓል። የኑሮ ሩጫ በሚበዛበት የከተማው ማዕከል እና መንግሥት ከእስላማዊ ነውጠኞች ጋራ ጦርነት ላይ በሚገኝበት ኹኔታ፣ በከተማው የሚገኙ ሕፃናት፣ በግጭቱ ምክንያት የተባባሰው የምግብ እጥረት ተጎጂዎች ኾነዋል።

ቢንቱ ሓሳን የተባለችው እናት፣ የሁለት ዓመት ልጇን ይዛ ሆስፒታል ተገኝታለች። ልጁ ተዳክሞና በደሙ ውስጥ የሚገኘው የስኳር መጠን እጅግ ቀንሶ ይታያል። ቢንቱ ብዙ አጥታለች። “አራት ልጆች ወልጄ ነበር። ሁለቱ ልጆቼ በአልሚ ምግብ እጥረት ምክንያት ሞተዋል። ሁለት ቀርተውኛል። ከእነርሱም አንዱ ታሟል። ወደ እዚኽ እንድመጣ ተነግሮኝ ነው የመጣኹት፤” ስትል፣ እያለፈችበት ያለውን የመከራ ንብርብር ታስረዳለች፡፡

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት እንደሚለው፥ ቦርኖ፣ አዳማዋ እና ዮቤ በተባሉ ግዛቶች፣ 700 ሺሕ የሚኾኑ ልጆች ከፍተኛ የተመጣጣኝ ምግብ እጥረት ገጥሟቸዋል።

በሰኔ እና በመስከረም ባሉት ወራት ውስጥ፣ ኹኔታው የከፋ እንደሚኾን ተ.መ.ድ አስጠንቅቋል። ይህ ወቅት ወትሮዎንም፣ ቀደም ብሎ የተመረተው ምግብ ክምችት የሚያልቅበት ነው። ባለፈው ዓመት የበልግ ወቅት በተከሠተው ከባድ ጎርፍ ምክንያት ደግሞ ምርቱ ተስተጓጉሏል።

ማቲያስ ሽሜል የተመድ አስተባባሪ ናቸው። “600 ሺሕ ሄክታር የእርሻ መሬት በመውደሙ እና ታጥቦ በመወሰዱ፣ በቅርብ ጊዜያት ውስጥ ከባድ የምግብ እጥረት ያጋጥማል፤” ሲሉ አመልክተዋል፡፡

ለሁሉም የሚዳረስ በቂ የምግብ ርዳታም የለም። ራን በተባለውና ከካሜሩን ጋራ በሚዋሰነው ሥፍራ፣ ለስምንት ወራት ርዳታ አለማግኘታቸውን ነዋሪዎቹ ይናገራሉ።

ኬሉ ሞዱ የተባለች ወላጅ፣ ያለበቂ ምግብ ልጆቿን ማጥባት እንደማትችል ትናገራለች። በመኾኑም ልጇ፣ በተመጣጣኝ ምግብ እጥረት ተጎድታለች። “ይህችን ልጅ በምወልድበት ወቅት በቂ የኾነ የጡት ወተት አልነበረኝም። ሕፃኗ ሽቅብ ይላትና ያስቀምጣት ጀመር፤” ትላለች፡፡

የምግብ እጥረቱ በከፊል የመጣው፣ ሩሲያ በዩክሬን ላይ በከፈተችው ጦርነት እና በሱዳን እየተካሔደ ባለው ግጭት ሳቢያ ነው።

ባለሥልጣናት እንደሚሉት ደግሞ፣ በናይጄሪያ የተከሠተው የዋጋ ግሽበት እና የገንዘብ ፖሊሲው፣ የሰዎችን ምግብ የመግዛት ዐቅም አዳክሟል።

ካራንቪር ሲንግ፣ በዩኒሴፍ የተመጣጣኝ ምግብ ሓላፊ ናቸው። እርሳቸው እንደሚሉት፣ ርዳታ ችግር ወዳለባቸው ሌሎች የዓለም ክፍሎች እየተላከ ቢኾንም፣ ናይጄሪያ አሁንም የምግብ አቅርቦት በማግኘት ላይ ናት። ሓላፊው አክለውም፣ “በዓለም

ላይ ባሉ ሌሎች አጠቃላይ አጣዳፊ ጉዳዮች ምክንያት፣ ርዳታ ወደዚያው እየተላከ ነው። ኾኖም ለጊዜው በቂ አለን። በቀጣይ ግን ተጨማሪ ርዳታ እንሻለን፤”

የናይጄሪያ ጸጥታ ኃይሎች፣ የእስላማዊ ነውጠኞቹን የመዋጋት ዐቅም እጅግ አዳክመዋል። አገሪቱ ግን አሁንም በጦርነት ላይ ናት። ያ እስከሚያቆም ድረስ፣ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች፣ ሌላ ዐይነት ጦርነት አለባቸው - ረኀብ።

XS
SM
MD
LG