በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

በተራረፉ የሆቴል ምግቦች ታግዘው - ከጎዳና ወደ ትምሕርት ቤት


ከጎዳና ላይ የተሰባሰቡት ተማሪዎች
ከጎዳና ላይ የተሰባሰቡት ተማሪዎች

ቤተክርስቲያን ደጅ ላይ ለልመና ላስቲክ አንጥፈው በሚያገኙት ትርፍራፊ ምግብ ለሚያሳድጓት ማየት የተሳናቸው ወላጆቿ በቶሎ ለመድረስ ጠንክራ ከምትማር የ10ኛ ክፍል የደረጃ ተማሪ ጀምሮ፤ ቤተሰቦቻቸውን ከነመፈጠራቸው የማያውቁ በልጅነት ጊዜያቸው ብዙ መከራን የገፉ ተማሪዎች ሕይወት በዚህ ዘገባ ውስጥ ተካቷል።

በተራረፉ የሆቴል ምግቦች ታግዘው - ከጎዳና ወደ ትምሕርት ቤት
please wait

No media source currently available

0:00 0:27:32 0:00

ከመናገሻዋ አዲስ አበባ በስተምስራቅ 515 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ሐረር ከተማ ቀበሌ 10 እና 16 እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ሁለት የተለያዩ የመኖሪያ ግቢዎች ይገኛሉ። ግቢዎቹ 25 ወንድና 15 ሴት ተማሪዎችን በአንድነት ይዟል። ተማሪዎቹ ከጎዳና ላይ የተሰበሰቡ ናቸው። አሰባሳቢው ደግሞ ከስምንት ዓመቱ ጀምሮ ብቸኝነትና የጎዳና ሕይወትን የቀመሰው የዛሬው መምሕር ተስፋ አለባቸው ነው። በሁለቱ መኖሪያ ግቢ ውስጥ ያሉት ተማሪዎች ሁሉም አሳዛኝ የልጅነት ታሪክ አላቸው። በሕፃንነት ዕድሜያቸው በድሕነትና በቤተሰብ እጦት መከራን የገፉ ለነገ ግን ብዙ ተስፋን የሰነቁ ናቸው። አንዳንዶቹ ደግሞ ተስፋ የመቁረጥ ስሜት የሚደመጥባቸውም ናቸው።

የጎዳና ተዳዳሪዎቹ ለአንድ ዓመት/2008 ዓ.ም/ በዚህ ሁኔታ ጎዳና ላይ እየኖሩ ነው ትምሕርታቸውን የተከታተሉት
የጎዳና ተዳዳሪዎቹ ለአንድ ዓመት/2008 ዓ.ም/ በዚህ ሁኔታ ጎዳና ላይ እየኖሩ ነው ትምሕርታቸውን የተከታተሉት

​የተማሪዎቹ የሕይወት ታሪክ የሚጀምረው ከድሕነትና ከቤተሰብ ማጣት ነው። አንዳንዶቹ በወላጆቻቸው የማሳደግ አቅም እጦት ምክንያት ለጎዳና ተዳርገው የነበሩ ናቸው። የአንዳንዶቹ ወላጆች ደግሞ ገና በልጅነት ዕድሜያቸው በሞት ተለይተዋቸዋል። የጥቂቶቹ እናቶች በሴተኛ አዳሪነት ንግድ ላይ የተሰማሩ በመሆናቸው ልጆቻቸውን ማሳደግ ሲያቅታቸው ወደ ጎዳና አውጥተዋቸዋል።አንዳንዶቹ ተማሪዎች እዛው ሐረር ከተማ የተወለዱ ናቸው። አንዳንዶቹ ደግሞ ከተለያየ ከተማ ነው ወደዛ የሄዱት። መብራቱ ታደሰ ከእነዚህ ተማሪዎች አንዱ ነው። በጉራጌ ዞን በቡታጅራ ከተማ የሚገኙ ቤተሰቦቹ በማሳደጊያ ማጣት ምክንያት ሐረር ለሚገኙ ዘመዶቻቸው ሰጡት።

መብራቱ ታደሰ 17 ዓመቱ ነው። 10ኛ ክፍል ጎበዝ ተማሪ ነው። ጎዳ
መብራቱ ታደሰ 17 ዓመቱ ነው። 10ኛ ክፍል ጎበዝ ተማሪ ነው። ጎዳ

“እንደ ልጆቻቸው ስለማያዩኝ እነሱን ጥዬ ወደ ጎዳና ወጣሁ” ይላል። መብራቱ ጎዳና ከወጣ ትምሕርቱን አላቋረጠም ቦቴ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ለሴተኛ አዳሪዎች ከሩቅ ቦታ ውሃ እየቀዳ ስለሚያመጣላቸው በሚሰጡት ገንዘብ እየታገዘ ትምሕርቱን ቀጠለ።

“በጎዳና ሕይወት ላይ ከፍተኛ ችግር ነበር። ምግብና ልብስ በጣም ቢቸግረንም እየተረዳዳን ኑሮን ገፍተነዋል” ይላል። እንደ መብራቱ ኹሉ ከሕፃንነት ጀምሮ እስከ አፍላው የወጣትነት ዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ወጣቶችም ነበሩ። ገና በስምንት ዓመት ዕድሜው የጎዳና ሕይወትን የቀመሰው ተስፋ አለባቸው እነዚህ ልጆች ለመርዳት ወስኖ ከአንድ ዓመት ተኩል በፊት ወደእነሱ ሄደ።ተስፋ አለባቸው የ26 ዓመት ወጣት ነው። ተወልዶ ያደገው ሐረር ከተማ ነው። በልጅነት ዕድሜው አባቱን አያውቀውም። እናቱ ከእርሱ አባት ልጅ መውለዷ ስላልተወደደላት ከቤተሰቦቿ ተነጥላ ብቻዋን ነበር ያሳደገችው።

ተስፋ አለባቸው ይባላል። በልጅነቱ ነው እናቱን የተነጠቀው። ለሰዎች በመላላክ ውሃ እየቀዳና ቆሻሻ እየደፋ ትምህርቱን ተምሮ አሁን 40 የጎዳና ልጆችን በአንድ ላይ አሰባስቦ ያስተምራል።
ተስፋ አለባቸው ይባላል። በልጅነቱ ነው እናቱን የተነጠቀው። ለሰዎች በመላላክ ውሃ እየቀዳና ቆሻሻ እየደፋ ትምህርቱን ተምሮ አሁን 40 የጎዳና ልጆችን በአንድ ላይ አሰባስቦ ያስተምራል።

“ለሊት ላይ ወደ ጅቡቲ ለሚጓጓዙ ተሽከርካሪዎች መንገድ ላይ ቆማ ለውዝ ትሸጥ ነበር። በዚህ ምክንያት በመጣ ቅዝቃዜ ሦስት ወር ታማ ሕይወቷ አለፈ። ያን ግዜ እኔ የአራተኛ ክፍል ተማሪ ነበርኩ።” የሚለው ተስፋ እናቱ የሞተችው እርሱ የስምንት ዓመት ልጅ እያለ ነበር። እናቱ ከሞተች በኋላ ማንም የሚያስጠጋው ዘመድ ስላለገኘ ቀደም ሲል ይኖሩበት በነበረው “አራተኛ” እየተባለ በሚጠራው ሰፈር መኖር ጀመረ።

የአካባቢው ነዋሪዎችና የገብርኤል ቤተክርስቲያን ሰንበት ትምሕርት ቤት ተማሪዎች እንዲሁም የሰፈር ጓደኖቹ ጭምር የሚሰጡትን ምግብ እየተመገበ እስከ ዐስራ ሦስት ዓመቱ ዘለቀ። ከዚህ ዕድሜ በኋላ ረዳት ማግኘት አስቸጋሪ ስለሆነበት ሥራ መሥራት እንደጀመረ ይናገራል። ምግብ ሳይበላ የሚውልበትና የሚያድርበት ቀን በርካታ እንደነበሩም ያስታውሳል።

“ጠዋት ትምሕርት ቤት ከመሄዴ በፊት ውሃ ቀድቼ እሄዳለሁ ስመለስ ደግሞ ቁሻሻ እደፋና ማታ መጥቼ አጠና ነበር።” የሚለው ተስፋ ከፍተኛ ጥረቶችን አድርጎ ዐስረኛ ክፍል ሲደርስ ወደ መምሕራን ማሰልጠኛ ገብቶ ትምሕርቱን ጨረሰ። በዚህ ሁሉ ጉዞ ውስጥ ዓላማ እንደነበረው ይናገራል።

“መጀመሪያ የምንኖረው ሥላሴ ቤተክርስቲያን ደጅ ነበር። ሰዎች ወደ ቤተክርስቲያን ሲመጡ ምግብ ይሰጡናል። እሱን እየበላን እኔና ወንድሜ ትምሕርት ቤት እንማር ነበር።”

“እኔ ባለፍኩበት መንገድ ሌሎች ማለፍ የለባቸውም የሚል ዓላማ ስለነበረኝ ጠንክሬ መሥራትና። መጀመሪያ አንድ ልጅ ከዛም ጠንከር ብዬ ሁለት ልጅ መጨመር እፈልግ ነበር” ተስፋ ያሰበውን አደረገ። እዛው ሐረር ከተማ ውስጥ መጀመሪያ አንዲት ልጅ ማስተማር ጀመረ። ጠንክሮ ሠርቶ ከግለሰብ እስከ ድርጅት በሐረር ከተማ ያገኘውን ሁሉ አስተባብሮ ጎዳና ላይ የሚገኙ ተማሪዎችን መርዳት ጀመረ። ሲጀምረው አንድ ጊዜ ብቻ ለመርዳት ነበር ነገር ግን ጠጋ ብሎ የሁሉንም ታሪክ ሲያዳምጥ እዛው ባሉበት ሆነው ትምሕርታቸውን እንዲቀጥሉ ማድረግ ጀመረ።

መብራቱ ከእነዚህ ተማሪዎች አንዱ ነው። ቢማር ውጤት ሊያመጣ እንደሚችል የገባው ከተስፋ ጋር ከተገናኘ በኋላ እንደሆነ ይናገራል። ተስፋ ተማሪዎቹ መጀመሪያ እዛው ባሉበት ትምህርት እንዲጀምሩ ነበር ያደረገው። ምግባቸውን በተመለከተ ደግሞ በሐረር ከተማ የሚገኙ ሆቴል ቤቶችን አነጋግሮ የተራረፉ ምግቦች በየተራ እንዲሰጧቸው ጠየቀ። ፈቃደኛ ሆኑላቸው።

“የተወሰኑ ሆቴሎች ንፁህ ምግብ ፈቅደው ለአንዳንድ ተማሪዎች የሚሰጡ አሉ። እኛ ደግሞ ዱሮ ቡሌ ከምናመጣበት ቦታ ሄደን እናመጣለን። የከሰዓት ተማሪ የኾኑት ለጠዋቶቹ ተማሪዎች ምሳ አምጥተው ይጠብቋቸዋል። የጠዋቶቹ ደግሞ ለከሰዓቶቹ ያመጣሉ።”.

መብራቱ ምግቡን በተመለከተ በየተራ ተረዳድተው እያመጡ መማር መቀጠላቸውን ይናገራል። “የተወሰኑ ሆቴሎች ንፁህ ምግብ ፈቅደው ለአንዳንድ ተማሪዎች የሚሰጡ አሉ። እኛ ደግሞ ዱሮ ቡሌ ከምናመጣበት ቦታ ሄደን እናመጣለን። የከሰዓት ተማሪ የኾኑት ለጠዋቶቹ ተማሪዎች ምሳ አምጥተው ይጠብቋቸዋል። የጠዋቶቹ ደግሞ ለከሰዓቶቹ ያመጣሉ።” ተስፋ በወቅቱ ከጎዳና ላይ ለሰበሰባቸው 89 ተማሪዎች የራሱን የሕይወት ታሪክ ስለነገራቸው በሐሳቡ ተስማምተው ጎዳና ላይ ዩኒፎርማቸውን እየለበሱ ደብተራቸውን አንጠልጥለው ወደ ትምህርት ቤት ሄዱ። ተስፋ በወቅቱ የነበረውን ሁኔታ ሲናገር "መጀመሪያ 89 ልጆችን ሰብስቤ ከሆቴል የተራረፈ ምግብ ተራ በተራ እያመጡ እሱን እየተመገቡ እንዲማሩ አደረኩ። ከእነዚህ ውስጥ አብዛኞቹ በተለያየ ምክንያት ትምሕርታቸውን አቋረጡ። አንዳንዶቹ በሴተኛ አዳሪነት ላይ የተሰማሩ ስለነበሩ በደረሰባቸው ከፍተኛ ችግር ምክንያት ትምሕርታቸውን መቀጠል አልቻሉም”

አርባዎቹ 25 ወንድና 15 ሴት ተማሪዎች ግን ጠንካራ ኾኑ። በዚህ ውስጥ ዕድሜያቸው ከስድስት እስከ 17 ዓመት የሆኑ ልጆች ይገኛሉ። ከክፍሏ አንደኛ ከአጠቃላይ ትምሕርት ቤቱ ሁለተኛ የወጣች የ11ኛ ክፍል ተማሪን ጨመሮ በትምሕርታቸው ጠንካራ የሆኑ ተማሪዎች አሉ።

እነዚህን ተማሪዎች ቆይታ የተቀላቀለችው የትነበርሽ አያሌው 16 ዓመቷ ነው። በሐረር ከተማ ነው ተወልዳ ያደገችው። የየትነበርሽ የልጅነት ታሪክ ለአንድ ልጅ ዕድገት የሚያስፈልገው በጣም ጥቂት ነገር እንኳን የተሟላበት አልነበረም። እናትና አባቷ ማየት የተሳናቸው ናቸው። ሁለቱም ሥላሴ በተባለ ቤተክርስቲያን ደጅ ላይ የላስቲክ ሸራ ወጥረው በልመና የሚያገኙትን ምግብ እየመገቡ ነው እሷንና ወንድሟን ያሳደጓቸው።

የትነበርሽ አያሌው 16 ዓመቷ ነው። እናቷም አባቷም ማየት የተሳናቸው ናቸው። ቤተክርስቲታ ደጅ ተቀምጠው እየለመኑ በሚያመጡት ምግብ ነው ያስተማሯት። ትምሕርት ቤት ከገባች ጀምሮ የ10ኛ ክፍል እስከደረሰች ድረስ የደረጃ ተማሪ ነች
የትነበርሽ አያሌው 16 ዓመቷ ነው። እናቷም አባቷም ማየት የተሳናቸው ናቸው። ቤተክርስቲታ ደጅ ተቀምጠው እየለመኑ በሚያመጡት ምግብ ነው ያስተማሯት። ትምሕርት ቤት ከገባች ጀምሮ የ10ኛ ክፍል እስከደረሰች ድረስ የደረጃ ተማሪ ነች

የትነበርሽ ስለ ዕድገቷ ስትናገር፤ “መጀመሪያ የምንኖረው ሥላሴ ቤተክርስቲያን ደጅ ነበር። ሰዎች ወደ ቤተክርስቲያን ሲመጡ ምግብ ይሰጡናል። እሱን እየበላን እኔና ወንድሜ ትምሕርት ቤት እንማር ነበር።” ጥረቷን የተመለከቱ በሐረር ከተማ ቀበሌ 08 ውስጥ “የድሆች ሰፈር” በሚባል ቦታ በትንንሹ የተከፋፈለ መጠለያ ቤት ተሰጠቷቸው ገቡ። “አባቴ ማየት ባይችልም በራሱ መሄድ ግን ይችላል። እናቴን የምመራት ግን እኔ ነበርኩ። ጠዋት እሷን ቤተክርስቲያን አድርሼ ወደ ቤት ተመልሼ እመጣና ልብሴን ቀይሬ ወደ ትምሕርት ቤት እሄዳለሁ። ትምሕርት ቤቱ ግን ራቅ ስለሚል እዛው እውላለሁ እናቴን ጎረቤቶች ያመጡልኛል።” ትላለች።

ትምሕርት ቤቱ ዩኒፎርም ስላለው ልብስና የመሳሰሉት ነገሮች አያስጨንቁኝም የምትለው የትነበርሽ በዚህ ሁኔታ እስከ ዘጠነኛ ክፍል ተማረች። በትምሕርት ቤት ውስጥ ደግሞ ጎበዝና የደረጃ ተማሪ ናት። ይህን የተመለከቱ ሰዎች ተስፋ ጋር አስገብተዋት አሁን እዛ ሆና የ10ኛ ክፍል ትምሕርቷን በመከታተል ላይ ትገኛለች። ስታድግ መሆን የምትፈልገው የሕክምና ባለሞያ ነው። የትነበርሽን ደጋግሜ ምን ቢሟላላት እንደምትፈልግ ጠየኳት መልሷ “ምንም አሁን ሁሉ ነገር ተሟልቶልኛል ነው።”

እሷን የሚያሳስባት ከጀመረችው ትምሕርቷ ሳትፈናቀል በቶሎ ለቤተሰቦቿ መድረስ ነው። የትነበርሽ ስድስተኛ ክፍል የሚማረው ታናሽ ወንድሟ ጠንክሮ እንዲያጠና የምትመክረውም ለዚህ እንደሆነ ነግራኛለች።

መንፈሳቸው ጠናካራ የሆኑ ተማሪዎች እንዳሉት ሁሉ ያለፉበትን መንገድ መናገር የሚከብዳቸው ልባቸው በሐዘን የተሰበሩ ተማሪዎች አሉ። ገሊላ ሰለሞን ከእነዚህ አንዷ ነች። ገሊላ አሁን የኮሌጅ ተማሪ ናት። የምትኖረው ሌላ ቦታ ነው ግን በተስፋ አማካኝነት ጥቂት የትራንስፖርት ርዳታ ታገኛለች። ተስፋ እንደነገረኝ ግቢ ውስጥ አስገብቶ ማስተማር የማይችለውን በውጭ ይረዳቸዋል። ሐረር የሚገኘው የሬፍት ቫሊ ኮሌጅ የነፃ የትምህርት ዕድል ሰጥቷት እየተማረች ነው።

ገሊላ ሰለሞን እናትና አባቷን በልጅነቷ ነው የተነጠቀችው አሁን የአንደኛ ዓመት የኮሌጅ ተማሪ ናት።
ገሊላ ሰለሞን እናትና አባቷን በልጅነቷ ነው የተነጠቀችው አሁን የአንደኛ ዓመት የኮሌጅ ተማሪ ናት።

“እናትና አባቴ በልጅነታችን ነው የሞቱት። እኔና ወንድሜ በየቦታው ተንከራተን ነው ያደግነው። እኔ ከልጅነቴ ጀምሮ በየሰው ቤት እየተንከራተትኩ ነው ያደኩት። ለሦስት ቀን ሳልበላ ትምሕርት ቤት የምሔድበት ቀን ነበር….” ገሊላ ስሜቷን አምቃ መናገር ያቅታታል።

“ቀኑን ሙሉ ነው የምንማረው ምግብ ስለማላገኝ ምሳ ሰዓት ሲደርስ ጓሮ እቀመጥና ወይም ደግሞ ላይብረሪ እገባና ውዬ እመጣለሁ። ስጨርስ እቤት ገብቼ ምግብ ካገኘሁ እበላለሁ ካጣሁ ደግሞ እተኛለሁ።” ገሊላ ትምሕርቷን የመጨረስ ጠንካራ ፍላጎት እንዳላት ደጋግማ ብትናገርም መከራዋ ጭንቀትን እንደፈጠረባት መሸሸግ ግን ትቸገራለች። በዚህ ላይ የነፃ ትምህርት ዕድሉን የሰጧት ኃላፊ በመቀየራቸው ዕድሏ በእንጥልጥል ላይ ነው። ተስፋ ልጆቹን ለማገዝ የወሰነው ከራሱ ታሪክ በተጨማሪ እንደ ገሊላ ያሉ በችግር እየተፈተኑ ለመማር የሚታትሩ ልጆችን ሲያይ ነው።

ግዮን ሽባባው በዚህ ግቢ ውስጥ የሚገኝ ሌላው ጎበዝ ተማሪ እንደሆነ ተነግሮናል። 17 ዓመቱ ነው 8ኛ ክፍል ነው።
ግዮን ሽባባው በዚህ ግቢ ውስጥ የሚገኝ ሌላው ጎበዝ ተማሪ እንደሆነ ተነግሮናል። 17 ዓመቱ ነው 8ኛ ክፍል ነው።

ግዮን ሽባባው በዚህ ግቢ ውስጥ የሚገኝ ሌላው ጎበዝ ተማሪ እንደሆነ ተነግሮናል። 17 ዓመቱ ነው 8ኛ ክፍል ነው። የተወለደው ቢሾፍቱ ከተማ ነው። እናቱ በልጅነቱ ነው የሞተችው። አባቱ ድሬደዋ ይገኛል ስለተባለ ወደዚያው አቀና። አልተሳካለትም። ወደ ሐረር ከተማ አቅንቶ ለጎዳና ሕይወት ተዳረገ።

“ግን እግዚያብሔር ይመስገን ጥሩ ጥሩ ሰዎች ያጋጥሙኛል። ትምህርት መማር አስጠልቶኝ ነበር ገፋፍተው ትምሕርት ቤት አስገቡኝ መጀመሪያ በትምሕርቴ ጠንካራ አልነበርኩም በኋላ ግን እየጠነከርኩ መጣሁ” ይላል አሁን በትምህርት ቤቱ የደረጃ ተማሪ ነው። በከተማው የሚገኙ የተለያዩ ሆቴሎች ተከፋፍለው ምግብ ይሰጧቸዋል። “ጠዋት ቁርሳችንን ዳቦ እንበላለን ምሳና እራታችንን ደግሞ ተራ በተራ ከየተመደብንበት ሆቴል እያመጣን እንበላለን።” የሚለው ግዮን ወደፊት ፖለቲካ ውስጥ ተሳትፎ አሻራውን ማስቀመጥ ወይም ደግሞ ታሪክ ማጥናት ያስደስተዋል።

ተማሪዎቹ ካለመብላት ወደ መብላት ከጎዳና ወደ መኖሪያ ቤት ስለገቡ ድምፃቸው ላይ የጥንካሬ መንፈስ ይሰማል። ተስፋ እንደሚለው ሁሉም ተማሪዎች ከትምሕርታቸው ጎን ለጎን የራሳቸው ተሰጦ አላቸው። መብራቱ ከእነዚህ አንዱ ነው። አሁን 10ኛ ክፍል ነው ከክፍሉ ሰባተኛ እንደሚወጣ ነግሮኛል። ኳስ መጫወት በጣም ስለሚወድ ከትምሕርቱ ጎን ለጎን በሐረር ከተማ በሚገኝ የእግር ኳስ ቡድን ውስጥ ገብቶ ኳስ ይጫወታል። ለዚህ ደግሞ ትልቁ ችግሩ ትጥቅ መሆኑን ይናገራል።

ተስፋ አለባቸው ከሚያስተምራቸው ልጆች ጋር
ተስፋ አለባቸው ከሚያስተምራቸው ልጆች ጋር

ተስፋ ለሁለቱ ግቢዎች በወር ዘጠኝ ሺሕ ብር ይከፍላሉ። ይህን ገንዘብ ከብዙ ሰዎች አሰባስበው እንደሚከፍሉ ነው የነገረን። ልጆቹን ለማሳደግ የማያንኳኳው በር የለም። የእነዚህን ተማሪዎች ትምሕርት ለማስጨረስ የቻለውን ያደርጋል። እቅድ እያወጣ ከምግብ እስከ ፅዳት አገልግሎት ርዳታ ይጠይቃል። ግቢ ውስጥ ያሉትን ተማሪዎች የሚያዩ የጎዳና ላይ ልጆች ደግሞ “እኛንስ መቼ ነው የምታስገባን?” በሚል ጥያቄ ወጥረው ይይዙታል። “በተለይ ዝናብ ሲጥል እዚህ አካባቢ መተው ቁጭ ሲሉ ሳይ መፈጠሬን እጠላለሁ” ይላል።

በዚህ ላይ አሁን መሰረት የያዙት ልጆቹ በተለያየ ምክኒያት እንዳይደናቀፉ ሁሌም ደግሞ ከተረጂነት ወጥተው ሠርተው መማር እንዲችሉ ልብስ ማጠቢያ ማሽን እና እንጀራ መጋገሪያ ቢያገኝ ተረዳድተው እንዲኖሩ ማድረግ እንደሚችል ይናገራል። በተጨማሪ ደግሞ የሚያጠኑበት መጽሐፍት እንዲሁም የግል ንፅህና መጠበቂያ ቁሶች ቢያገኙ ብዙ ነገሮች እንደሚያቃልልላቸው ይናገራል።

የእርሱ የዘወትር ጭንቀት እንዲህ ያሰባሰባቸው ጎበዝ ተማሪዎች ያሰቡበት ሳይደርሱ በአጭር እንዳይቀሩ ነው። “ባለንበት ከተማ ሁሉም የራሱን ኑሮ ለማሸነፍ የሚታገልበት ቢሆንም የቻልነውን ሁሉ ጥረት አድርገን ልጆቹን ትምሕርት ለማስጨረስ ከፍተኛ ጥረት አደርጋለሁ” ብሏል።

ተስፋና ተማሪዎቹ “እስካሁን እዚህ የደረስነው በእነርሱ ድጋፍ ነው “ በማለት ደጋግመው የሐረር ከተማን ሕዝብ ያመሰግናሉ።

የፌስቡክ አስተያየት መስጫ

XS
SM
MD
LG