በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ከብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤት የተሰጠ መግለጫ


ብሄራዊ የደህንነት ምክር ቤት በ08/01/2011 ዓ.ም ባደረገው ስብሰባ በአገራችን እየተስተዋሉ ያሉ ህገ-ወጥና የስርዓት አልበኝነት እንቅስቃሴዎችን ገምግሞ የሚከተለውን መግለጫ አውጥቷል።

ብሄራዊ የደህንነት ምክር ቤት በ08/01/2011 ዓ.ም ባደረገው ስብሰባ በአገራችን እየተስተዋሉ ያሉ ህገ-ወጥና የስርዓት አልበኝነት እንቅስቃሴዎችን ገምግሞ የሚከተለውን መግለጫ አውጥቷል።

ባለፉት አምስት ወራት የዴሞክራሲ ምህዳርን ለማስፋት በርካታ ስራዎች ተከናውነው ተስፋ ሰጪ ውጤቶች ተገኝተዋል። በዚህም መላው ህዝባችን ከመቼውም ጊዜ በላይ በአገሩ ተስፋ እንዲሰንቅና በሃገሩ መጻዒ እድል ላይ የራሱን አስተዋፅኦ ለማበርከት እንዲነሳሳ አድርጓል።

ሆኖም ግን የዲሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ከህግ የበላይነት ውጭ የሚታሰብ አለመሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ በለውጥ ውስጥ እንደመሆናችን መጠን መንግስት ችግሮችን በሀይል ለመፍታት ከመሞከር ይልቅ ሆደ ሰፊነትን ቢያሳይም ይህን እንደ አቅመ ቢስነት የተመለከቱ የጥፋት ሀይሎች የወጣቱን ስሜት በማነሳሳት የሚፈፅሟቸው ወንጀሎች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሱና እየተበራከቱ መጥተዋል።

ሰሞኑን በአዲስ አበባና በዙሪያዋ በተከሰቱ ግጭቶች በርካታ ዜጎች ውድ ህይወታቸውን አጥተዋል። ይህን ብጥብጥ በተለያዩ አካባቢዎች ለማስቀጠል፣ በሱማሌ ክልልና በሌሎች አካባቢዎች የከሸፈባቸውን የጥፋት አቅድ በሌላ ሙከራ ለመቀጠል እንዲሁም በመስከረም መጨረሻ የሚካሄደውን የኢህአዴግ ጉባኤ ለማደናቀፍ በርካታ ጥረቶች እየተደረጉ ነው።

ሁከቱ ከላይ እንደሚመስለው በትናንሽ ችግሮችና ልዩነቶች የሚነሳ ሳይሆን በታቀደ መልኩ የሚከናወን፣ ድብቅ ፖለቲካዊ ዓላማ ያለው፣ ህዝብን ከህዝብ በማጋጨት ወይም ግጭቶች ሲከሰቱ እነሱን እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም የማባባስ እና ሃገራችንን የማያባራ ግጭት ሰለባ በማድረግ ለውጡን ለማሽመድመድና ለመቀልበስ የሚደረግ ሴራ አካል ነው።

በመሆኑም መንግስት ያለበትን የህግ የበላይነትና የዜጎችን ደህንነት የማስጠበቅ ሃላፊነት ለመወጣት ማንኛውንም ህጋዊ፣ የማያዳግምና ተገቢ እርምጃ ለመውሰድ በሙሉ ዝግጅትና አቋም ላይ እንደሆነ ሊታወቅ ይገባል። ስርዓት አልበኝነትን ከዚህ በኋላ የምንታገስበት ልብ፣ የምንሸከምበት ትከሻ የለንም። በመሆኑም ለዜጎች ህይወት ዋስትና ለመስጠት መንግስት ማንኛውንም ህጋዊና የማያዳግም እርምጃ መውሰድ የጀመረ ሲሆን ይህ ሁኔታ ተጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል።

ወጣቱም በስሜት እየተገፋፋ፣ የፖለቲካ ነጋዴዎችና ዘራፊዎች መሳሪያ እየሆነ አፍራሽ ወደሆነ ድርጊት መምጣቱን መረዳት ይኖርበታል፡፡ በመሆኑም አውቆም ይሁን ሳያውቅ በህገ-ወጥ ድርጊት ላይ የሚሳተፍ ወጣትና ማንኛውም የህብረተሰብ ክፍል ህጋዊ እርምጃ የሚወሰድበት መሆኑን አውቆ ከጥፋት ተግባሩ እንዲሰበሰብ መንግስት ያሳስባል፡፡

የጥፋት ሀይሎች በሚያደርጉት የመጨረሻ መፍጨርጨር ለጊዜው የታወከው የህዝብ ሰላም ወደ ነበረበት እንደሚመለስ መንግስት እያረጋገጠ በየትኛውም የኢትዮጵያ ክፍል ኢትዮጵያዊ የሆነ ሁሉ የደህንነት ስሜት ተሰምቶት መንቀሳቀስና መኖር እስከሚችል ድረስ፥ መንግስት ሰላምና መረጋጋትን የማስከበር ስራውን አጠናክሮ ይቀጥላል።

በዚህ ሂደት ውስጥ ወንጀሎቹን በማቀነባበር ደረጃም ሆነ ለተቀነባበሩ ወንጀሎች መሳሪያ ሆኖ የተገኘ ሰው፣ በማንኛውም ደረጃ ወንጀል ላይ የተሳተፈ አካል ከህግ-ሊያመልጥ አይችሉም፤ ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ በህግ ተጠያቂ ይሆናል። በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ልዩነትን በሚያሰፉና ብጥብጥን በሚፈጥሩ እንቅስቃሴዎች ላይ ተሳትፎ የሚያደርጉ አክቲቪስቶችና የፖለቲካ ፓርቲዎች እጃሁን መሰብሰብ ይኖርባችኋል፡፡

በመጨረሻም፥ አሁን ከጀመርነው የሰላምና የዴሞክራሲ የለውጥ መንገድ ማንም ሀይል ሊያደናቅፈን እንደማይችል ልናረጋግጥላችሁ እንወዳለን።

መስከረም 8 ቀን 2011 ዓ.ም

የኢፌዴሪ ብሄራዊ የደህንነት ምክር ቤት

አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ

ከብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤት የተሰጠ መግለጫ
please wait

No media source currently available

0:00 0:04:21 0:00

የፌስቡክ አስተያየት መስጫ

XS
SM
MD
LG