የፈረንሳይ ኃይሎች ከምዕራብ አፍሪካዊቷ ቻድ ሙሉ ለሙሉ ለቀው ወጥተው መጨረሳቸውን የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት ማሃማት ኢድርስ በደስታ ተቀብለውታል። ይህም ፈረንሳይ ጂሃዲስት ታጣቂዎች በስፋት ከሚንቀሳቀሱበት የአፍሪካ ሳህል ቀጠና የመውጣቷ ሂደት የመጨረሻው ምዕራፍ ነው ተብሏል።
ከአንድ ቀን በፊት በዋና ከተማው ን'ጃሚና በዝግ በተካሄደ ወታደራዊ ስነስርዓት ዴቢ ለቻድ ኃይሎች እና ዲፕሎማቶች ንግግር ያደረጉ ሲሆን፣ ፈረንሳይ በመካከለኛው አፍሪካውቷ ሀገር የነበራትን የመጨረሻ የጦር ሰፈር አስረክባለች። ቻድም ከቀድሞ ቅኝ ገዢዋ ጋር የነበራትን ወታደራዊ ትብብር ሙሉ ለሙሉ አቋርጣለች።
ከዚህ በኃላ የቻድ ባንዲራ ብቻ በሚውለበለብበት የጦር ሰፈር ሆነው ንግግር ያደረጉት ዴቢም፣ ከፈረንሳይ ጋር ያለንን ወታደራዊ ትብብር ብናቋርጥም፣ ግንኙነታችንን ግን እንቀጥላለን ብለዋል።
አክለውም ቻድ የበለጠ ጠንካራ እና የተሻለ ጦር እንደምትገነባ እና በመከባበር፣ እንዲሁም ነፃነትን እና በሉዓላዊነትን በአማከለ መልኩ አዳዲስ ትብብሮችን እንደምትፈጥር አመልክተዋል።
ቻድ ከቅኝ ግዛት ነፃ መሆኗን ካወጀችበት እ.አ.አ 1960 አንስቶ፣ የፈረንሳይ ወታደሮች እና ተዋጊ አውሮፕላኖች በቻድ ቋሚ መቀመጫ የነበራቸው ሲሆን፣ የቻድን ጦር በመገንባት እንደረዱ ተመልክቷል። በተለይ ፈረንሳይ በማሊ፣ በቡርኪናፋሱ እና ኒጀር የተደረጉትን መፈንቅለ መንግስቶች ተከትሎ ከሀገራቱ እንድትወጣ ስትደረግ፣ በሳህል ቀጠና ውስጥ የነበራት ብቸኛው ትስስር የቻድ ጦር ሰፈር ነበር።
መድረክ / ፎረም